ዲ/ን መርሻ አለኸኝ(ዶ/ር)
የቅዱስ ያሬድን 1500ኛ የልደት በዓልን ምክንያት በማድረግ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የተዘጋጀ ዐውደ ጥናት በግዮን ሆቴል ሳባ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተከፈተ፡፡ በዐውደ ጥናቱ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያዎች ሓላፊዎች፣ በዋና ዋና አብነት ት/ቤቶች የሚያስተምሩ መምህራንና የመንግሥትና ልዩ ልዩ ተቋማት ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንት ተገኝተዋል፡፡
ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ማኅበሩ ቅዱሳት መካናት ራሳቸውን ችለው የሚተዳደሩባቸውን ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽና በመተግበር ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች ድጋፍ በማድረግ ከፍተኛ ሥራ አየሠራ እንደኾነ ከገለጹ በኋላ፤ ሊቁ ለሀገራችን ከሰጠው አበርክቶ አንጻር ማኅበሩ ከፍተኛ ቦታ የሚሰጠውን የቅዱስ ያሬድን የ1500ኛ ዓመት የልደት በዓል በሰፊ ዝግጅት ለማክበር እንደወሰነ ገልጸዋል፡፡