Monday, October 14, 2013

ጸሎት


መጋቢት 18/2004 ዓ.ም.
በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ
ጸሎት ጸለየ፡- ለመነ፣ ጠየቀ አማለደ፣ ማለደ ካለው የግዕዝ ቃል የወጣ ቃል ነው፡፡ ጸሎት ማለት ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር እግዚአብሔርን ማመስገን መለመን፣ መጠየቅ፣ መማለድ፣ መማፀን ነው፡፡ “ጸሎት ብሂል ተናግሮ ምስለ እግዚአብሔር፡፡” አባታችን አዳምም ከመላእክት ተምሮ በየሰዓቱ ይጸልይ ያመሰግን ነበር፡፡ ዲያብሎስ በእባብ አድሮ ወደ አዳም በመጣ ጊዜ ጸሎት እያደረገ ስለነበር ዲያብሎስን ድል ነሥቶታል ሔዋንን ግን ሥራ ፈትታ እግሯን ዘርግታ ስለአገኛት ድል ነስቷታል፡፡
ጸሎት ሰማእታት ከነደደ እሳት፣ ከተሳለ ስለት፣ ከአላውያን መኳንንት፣ ከአሕዛብ ነገሥታት ከዲያብሎስ ተንኮል እና ሽንገላ ዲያብሎስ በእነርሱ ላይ ከአጠመደው አሽከላ የዳኑበት ጋሻ ነው፡፡ ኤፌ.6፥10 21 ጸሎት፣ ሰው አሳቡን ለእግዚአብሔር የሚገልጥበት እግዚአብሔርም የሰውን ልመና ተቀብሎ ፈቃዱን የሚፈጽምበት ረቂቅ ምስጢር ነው፡፡
የጸሎት መሠረቱ “ዕሹ ታገኛላችሁ ለምኑ ይሰጣችኋል ደጁ ምቱ ይከፈትላችኋል” የሚለው የጌታችን ትምህርት ነው ማቴ.7፥7
ጸሎት፡- በሦስት ክፍል ይከፈላል
  1. ጸሎተ አኰቴት
  2. ጸሎተ ምህላ
  3. ጸሎተ አስተብቊዖት
  1. ጸሎተ አኰቴት፡- ማለት እግዚአብሔርን ከሁሉም አስቀድሞ ስለተደረገልን ነገር በማመስገን የሚጀመር ጸሎት ነው ይህም ዓይነት ጸሎት የቅዱስ ባስልዮስን የምስጋና ጸሎት የመሰለ ነው፡፡
“ነአኲቶ ለገባሬ ሠናያት ላዕሌነ እግዚአብሔር መሐሪ”
“ለእኛ በጎ ነገርን ያደረገ ይቅርባይ እግዚአብሔር አምላካችንን እናመሰግነዋለን” ይልና ምክንኀያቱን ሲገልጥ ጠብቆናልና፥ አቅርቦናልና፥ ወደ እርሱም ተቀብሎናልና፥ እስከዚችም ሰዓት አድርሶናልና” ይላል፡፡ /ሥርዐተ ቅዳሴ/ ይህ ጸሎት የምስጋና ጸሎት /ጸሎተ አኰቴት/ ይባላል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህንን የምስጋና ጸሎት ለፊልጵስዮስ ክርስቲያኖች ሲጽፍላቸው “ነገር ግን በሁሉ ነገር ጸልዩ ማልዱም እያመሰገናችሁም ልመናችሁን ለእግዚአብሔር ግለጡ” ይላል፡፡ ፊል.4፥6 ዳግመኛም “ስለእናንተ በኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለእናንተ ስለተሰጣችሁ ጸጋ ዘወትር እግዚአብሔርን አመስግነዋለሁ” 1ቆሮ.1፥4 ብሎ ከመለመን አስቀድሞ እግዚአብሔርን ማመስገን አስፈላጊ መሆኑን አስተምሯል፡፡ በዚህ መሠረት ሰው የተደረገለትን በጎ ነገር ሁሉ በማሰብ ፈጣሪውን ማመስገን ከማመስገንም ቀጥሎ የሚያስፈልገውን ከፈጣሪው መለመን አስፈላጊ ነው፡፡
ከቅዱስ ጳውሎስ የምንማረው ለእኛ ስለተደረገልን ብቻ ማመስገንን አይደለም፤ ሌሎች ስለተደረገላቸውም ማመስገን ተገቢ መሆኑን እንጂ፡፡ “ለእናንተ ስለተሰጣችሁ ጸጋ ዘወትር እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ” ሲል ለወገኖቹ ስለተደረገላቸው በጎ ነገር በደስታ ማመስገኑ ነው፡፡ ክርስትና ማለት ለእኔ ብቻ ማለት ሳይሆን ለሌሎችም መኖር፣ ለሌሎች በተደረገው የእግዚአብሔር ስጦታም ደስ መሰኘት ነው፡፡ ይህን የምስጋና ጸሎት /ጸሎተ አኮቴት/ ብዙ አባቶች፣ እናቶች ተጠቅመውበታል፡፡ ለምሳሌም ያህል ዘካርያስንና ኤልሳቤጥን መመልከት እንችላለን፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥ እግዚአብሔር ያደረገላትን በጎ ነገር ስትመሰክር “እግዚአብሔር በዚህ ወራት ከሰው ስድቤን ያርቅ ዘንድ በጎበኘን ጊዜ እንዲህ አደረገልኝ” ብላለች፡፡ ሉቃ.1፥25 እግዚአብሔር ጎበኘኝ ብላ ቸርነቱን አደረገለኝም በማለት የተደረገላትን መልካም ስጦታ ዮሐንስን መጽነሷን ገልጣ አመስግናለች፡፡ ዘካርያስም እንዲሁ አመስግኗል፡፡ “ያን ጊዜም አፉ ተከፈተ አንደበቱም ተናገረ እግዚአብሔርንም አመሰገነ” ሉቃ.1፥65 “ከዚህ ጊዜ ያደረስከኝ፥ ከደዌ የፈወስከኝ፥ ዮሐንስን የሰጠኸኝ ብሎ ፈጣሪውን አመስግኗል በመቀጠልም ይቅር ያለን ለወገኖቹም ድኅነትን ያደረገ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን ከባሪያው ከዳዊት ቤት የምንድንበትን ቀንድ አስነሣልን፡፡” ሉቃ.1፥68 በዘካርያስ ጸሎት ውስጥ ምስጋናውን አስቀድሞ ትንቢቱን አስከትሎ እናገኘዋለን፡፡ በዚህ ምስጋናውና ትንቢቱ አምላክ ለእኛ ያደረገው የቤዛነቱን ሥራ በመግለጥ ሲያመሰግን እንመለከታለን፡፡
2. ጸሎተ ምህላ፡- ጸሎተ ምህላ ስለፈውሰ ሕሙማን …… ስለ ሀገርና ስለነገሥታት ስለ ጳጳሳት፣ ካህናት ዲያቆናት፣ ምዕመናን ሕይወት ቸነፈር፣ ጦርነት፣ ረሀብ፣ ድርቅ ወይም ሌላ አስጊ ነገር በሆነ ጊዜ በብዛት፣ በማኅበር የሚጸለይ ጸሎት ነው፡፡ የምህላ ጸሎት ሲጸለይ በእስራኤል ላይ ቸነፈር በተነሣ ጊዜ አሮን በሽተኞን ባንድ ወገን ጤነኞችን ባንድ ወገን አድርጎ የክህነት ልብሱን ለብሶ ማዕጠንተ ወርቁን ይዞ በራስህ የማልክላቸውን አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብን አስበህ የወገኖችህን ኀጢአት ይቅር በል”  እንደጸለየላቸው ነው፡፡ ዘኁ.16፥46-50

ዛሬም ካህናት ከጠቀስናቸው አስጊ ነገሮች ማንኛውም በሀገር ላይ ቢመጣ ወደ ሀገር እንዳይገባ ገብቶ ቢሆን ከፍ ያለ ጉዳት እንዳያመጣ የክህነት ልብስ ለብሰው ማዕጠንቱ ይዘው ሥዕለ ማርያም፣ መስቀል አቅርበው ማኅበረ ክርስቲያንን ሰብስበው፣ ኢየሱስ ክርስቶስን “ስለእኛ ከድንግል ማርያም መወለድህን ስለእኛ መሠቀል መሞትህን አስበህ የህዝብን ኀጢአት ይቅር በል ከመዓት ወደ ምሕረት ተመለሰ” እያሉ በምህላ ይጸልያሉ፡፡

የምህላ ጸሎት መአትን መቅሰፍትን ይመልሳል ጦርን፣ ቸነፈርን ያስታግሳል መሠረቱም፡፡
“ጾም ለዩ ምህላ ስበኩ” ያለው ቃል ነው፡፡ ይህ ጸሎት በሰላም ጊዜ ሰላሙ ዘላቂ እንዲሆን በጦርነት ጊዜ ለመከላከያነት ዋና መሣሪያ ነው፡፡ ስለዚህ አጥብቀን ልንከተለው ይገባል፡፡

የምህላ ጸሎት ነገሠታት ከዙፋናቸው ወርደው ወንድ ሙሽራ ሴት ሙሽራ ከጫጉላቸው፣ ከመጋረጃቸው ለምግብ የደረሱ ልጆች ከምግብ ለምግብ ያልደረሱ ከጡት ተከልክለው ሕዝብ ሁሉ ምንጣፍ ለብሰው አመድ ነስንሰው የሚጸልዩት ከፍተኛ ጸሎት ነው ኢዩ.2፥12-18፣ ዮና.3፥5

3.    ጸሎተ አስብቊዖት
ይህ ጸሎት አንድ ሰው ስለሚፈልገው ነገር ቦታ ለይቶ ሱባኤ ገብቶ የሚጸልየው ጸሎት ነው፡፡ ይህ ጸሎት በተለይ ጣዕመ ጸጋን በቀመሱ በተባሕትዎ፣ በምናኔ በገዳም በሚኖሩ አበው ዘንድ የተለመደና የሚደረግ ጸሎት ነው፡፡ ወጣንያን እግዚአብሔርን ጠይቀው አድርግ አታድርግ የሚል መልስን አይጠብቁም፡፡ ፍጹማን አባቶች ግን እግዚአብሔር ጠይቀው አድርግ ወይም አታድርግ የሚል ፈቃደ እግዚአብሔርን ሳይቀበሉ የሚያደርጉት ነገር የለምና ቦታ፣ ጊዜ ወስነው ፈቃደ እግዚአብሔር ይጠይቃሉ፡፡ ይህ ጸሎተ አስተብቊዖት ይባላል፡፡ ይህም ማለት መላልሶ ደጋግሞ ያለ ዕረፍት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ የሚደረግ ጸሎት ነው፡፡ ለምሳሌ ትልቁ መቃርስ ዓለምን ዞሮ ለመጎብኘት ለተከታታይ አምስት ዓመታት እግዚአብሔርን ከለመነ በኋላ እየዞረ መካነ ቅዱሳንን እንዲጎበኝ ከእግዚአብሔር ፈቃድ አግኝቷል በዚህም ከእርሱ ከገድል በትሩፋት የሚበልጡ መናንያን በማግኘቱ መነኮሳትማ እነርሱ እንጂ እኔ ምንድን ነኝ? እያለ ራሱን እየወቀሰ እንደተመለሰ በመጽሐፈ መነኮሳት ተጽፎ እናገኛለን፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን “መስተበቊዕ” የሚባል የጸሎት ክፍል፡፡ አለ ይህ ጸሎት በካህናት አባቶቻችን ስለሙታን፣ ስለሕያዋን፣ ስለነገሠታት፣ ስለ ጳጳሳት ስለ ንዑሰ ክርስቲያን፣ ስለ ምእመናን መባዕ ስለሚያቀርቡ ስለነጋድያን፣ ስለዝናም ስለ ወንዞች የሚጸለይ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የጸሎት ክፍል ነው፡፡

ጠቅላላውን በቤተ ክርስቲያን የሚጸልዩ ጸሎታት ጸሎተ ፍትሐት፣ ጸሎተ ተክሊል፣ ጸሎተ ህሙማን፣ ጸሎተ ቅዳሴ፣ ጸሎተ ሰዓታት፣ የግል ጸሎት፣ የማኅበር ጸሎት እነዚህ ሁሉ ከላይ ከዘረዘርዓቸው ሦስቱ የጸሎት ክፍሎች አይወጡም፡፡ ከጸሎተ አኰቴት ከጸሎተ ምህላ፣ ከጸሎተ አስተበቊዖት ይመደባሉ፡፡ እነዚህን ጸሎታት በሰቂለ ኅሊና በአንቃዕድዎ /ዐይንን ወደ እግዚአብሔር በማንሳት/ መጸለይ ታላቅ ዋጋ የሚያሰጥ ከሰይጣን ወጥመድ የሚታደግ ሕይወትን የሚስተካከል ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቅ አጋንንትን የሚያርቅ ኀይለ እግዚአብሔርን ለሚጸልየው የሚያስታጥቅ መላእክትን የሚያስመስል ነው፡፡

እኛም ሰውነታችን ከበደል ልቡናችን ከቂም ከበቀል እንዲሁም ከተንኮል ንጹሕ አድርገን ብንጸልይ እንጠቀማለን ጸሎታችን ተሰሚ ልመናችንና ጩኸታችን ግዳጅ ፈጻሚ ይሆናል፡፡ የአባቶቻችን ጸሎት የተቀበለ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታችንን ይቀበለናል፡፡

ይቆየን

Wednesday, September 4, 2013

የዘመን አቆጣጠር ባሕረ ሐሳብ

Source: Dn. Melaku Ezezew

1. ባሕረ ሐሳብ ማለት ምን ማለት ነው?

ባሕረ ሐሳብ ማለት ቁጥር ያለው ዘመን ማለት ነው፡፡ በሌላ አገላለጽም የሐሳብባሕር ማለት ነው፡፡ በዓላት እና አጽዋማትን ለማውጣት የመደመር፣ የመቀነስ፣የማባዛት ስሌትን ብቻ ሳይሆን ሐሳበ ፀሐይን፣ ሐሳበ ወርኅን፣ ሐሳበ ከዋክብትን ሐሳበዐበቅቴን ወዘተ አጠቃሎ የያዘ እንደ ባሕር የሰፋ በመሆኑ የሐሳብ ባሕር ተብሏል፡፡የዘመን አቈጣጠር ማለት ስለማሕበራዊ ኑሮ ጠቄሜታና የሃይማኖት ተግባሮችለማከናወን በሚያገለግል መልኩ ተፈጥሮአዊውን የወቅቶች ክፍፍል እርስ በርሳቸውየማመቻቸት ዘዴ ነው፡፡
ማርቆስ ወንጌላዊ

ሐሳበ ዘመን የዘመን አቆጣጠርማለት ሲሆን የሐሳበ ዘመን ትምህርትባሕረ ሐሳብ ይባላል፡፡ ባሕረ ሐሳብየሚለው ቃል ሐሰበ ቆጠረ ከሚለው ግስየወጣ ዘመድ ዘር ነው፡፡ ስለዚህ ባሕረሐሳብ ማለት ቁጥር ያለው ዘመን ወይምዓመተ ዓለም ማለት ነው፡፡ ባሕረሐሳብ መባሉም የባሕር አዝዋሪቱ፣መንገዱን፣ ጥልቀቱና ስፋቱ ረዥምናሰፊ እንደሆነ የባሕረ ሐሳብ ትምህርትምመንገዱን ስፋቱ ልዩ ልዩ በሆነየአጽዋማትና የሱባዔያት ምሥጢርየተሰናዳ ስለሆነ ነው፡፡

Wednesday, August 7, 2013

ጾመ ፍልሰታ

 IN THE NAME OF THE FATHER AND THE SON AND THE HOLY SPIRIT, ONE GOD.  AMEN.



''Filseta'' is a pre-assumption fast instituted by the apostles. It lasts for 15days and is commonly refferd as ''little lent''. It is a sober and earnest time in which people of all age participate. Even small children under seven years of age, the sick, and the sojourner, who are normally exempt from the discipline, maintain the fast of the assumption. Apostles continued to be sad and sorrowful, because of her separation from them, and because they were left orphans by her; for Our Lord had given them the hope that they would see her in the flesh. The Ethiopian book of saints-the synaxarium /January 29/ discusses the assumption. Filseta is the time when the faithful examine their lives in light of the purity, holiness, and obedience of the Virgin. In this spirit one fasts,one prays,one dedicates anew his or her life to God.

“ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፥8/

“ተንሥኢ ወንዒ ቅርብትየ እንቲአየ ሠናይት ርግብየ ውስተ ጽላሎተ ኰኲሕ ቅሩበ ጥቅም፡፡ አቅራቢያዬ መልካሟ ርግብየ ተነሽ፤ ነዪ፤ በግንቡ አጠገብ ወዳለው ወደ ዋሻው ጥላ፡፡” /መኃ.2፥10-14/

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እመቤታችንን መቅደሱ፥ ታቦቱ፣ ማደሪያው፣ መንበሩ እናቱ አድርጎ መረጣት፡፡ ስለዚህ ምክንያት አብ ጠበቃት ወልድ በተለየ አካሉ ሥጋን ከርሷ ተዋሐደ መንፈስ ቅዱስ አጸናት፡፡ እመቤታችን በዚህ ኃላፊ ዓለም ለ64 ዓመት ቆይታለች፡፡ ጥር ሰኞ ይብታል ሰኞ እስከ ሰኞ 8 ሰኞ እስከ ሰኞ 15፣ ሰኞ እስከ ሰኞ 22፣ ሰኞን ትቶ እሑድ ጥር 21 ቀን እመቤታችን አርፋለች፡፡ ሐዋርያት ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡ ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡

Tuesday, July 30, 2013

የአብርሃም ዛፍና የአብርሃም ድንኳን

በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ
ነገረ ማርያም በብሉይ ኪዳን ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ 



እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ለአብርሃም በአንድነት በሦስትነት በተገለጠባት ዛፍና፤ በገባበት ድንኳን ትመሰላለች (ዘፍ ፲፰፥፩-፴፫)፡:

ይኸውም አብርሃም ከደግነቱ ብዛት እንግዳን ከመውደዱ የተነሣ ድንኳኑን በተመሳቀለ ጎዳና ሠርቶ የወጣ የወረደውን ያለፈ ያገደመውን ሲቀበል የሚኖር በሥራው ኹሉ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ጻድቅ ነበር (ሮሜ ፬፥፩-፫)፡፡ ጽድቁም ሊታወቅ ስድስት ሰዓት ላይ አብርሃም በድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ ሳለ፤ በመምሬ ዛፍ ሥር እግዚአብሔር በአንድነት በሦስትነት ተገለጸለት ‹‹ወሶበ አልዐለ አብርሃም አዕይንቲሁ ነጸረ ሠለስተ ዕደወ እለ ይቀውሙ ወርእየ ወሮጸ ለተቀብሎቶሙ እምኆኅተ ኅይመት ወሰገደ ውስተ ምድር›› ይላል ዐይኑን አቅንቶ ሲመለከት፤ ሥላሴ በአምሳለ ዕደው ቆመው አይቶ፤ ሊቀበላቸው ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ሮጠ፤ ወደ ምድርም ሰገደ፤ ከዚኽ በኋላ ‹‹አቤቱ በፊትኽስ ሞገስ አግኝቼ እንደኾነ ባሪያኽን አትለፈኝ ብዬ እለምናለኍ፤ ጥቂት ውሃ ይምጣላችኍ፤ እግራችኹን ታጠቡ፤ ከዚኽችም ዛፍ በታች ዕረፉ…›› በማለት ተናግሯል፡፡ ‹‹በፊትኽ ሞገስን አግኝቼ›› ብሎ አንድነታቸውን፤ ‹‹ውሃ ይምጣላችኍ›› ብሎ የሦስትነታቸውን ምስጢር ገልጾአል፡፡

ይኽቺ አንድነቱ ሦስትነቱን ሳይጠቀልለው ሦስትነቱ አንድነቱን ሳይከፍለው በአንድነት በሦስትነት የሚመሰገን እግዚአብሔር የተገለጠባት ዛፍ፤ አንድነት ሦስትነት በጐላ በተረዳ ነገር የታወቀባት ከሦስቱ አካል አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድን በድንግልና የወለደች የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ መኾኗን፤ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ እንዚራ ስብሐት መጽሐፉ ላይ
....‹‹አንቲ ውእቱ ዕፀ ድርስ ዘለአብርሃም በርስአኒሁ
....ዘብኪ አጽለለ እግዚአብሔር በሥላሴሁ ››
(ለአብርሃው በእርጅናው ወቅት፤ እግዚአብሔርን በሦስትነት ያስጠለለብሽ የወይራ ዕንጨት አንቺ ነሽ) በማለት ሲገልጥ፤ ዳግመኛም በዚኹ መጽሐፉ፡-

...‹‹እንቲ ውእቱ ዕፀት ዘነበርኪ ጥቃ ኀይመት፣
...ዘብኪ አጽለሉ ሠለስቱ አጋዕዝት››
(ባንቺ ሦስቱ ጌቶች (ሥላሴ) የተጠለሉብሽ በድንኳን አጠገብ የቆምሽ ዕንጨት አንቺ ነሽ) በማለት በአንድነቱ ምንታዌ (ኹለትነት)፣ በሦስትነቱ ርባዔ (አራትነት) ለሌለበት አምላክ የሦስትነቱ የአንድነቱ ምስጢር መገለጫ የሥላሴ ማደሪያ መኾኗን መስክሯል፡፡

Sunday, June 23, 2013

ጰራቅሊጦስ

በቤካ ፋንታ

  • እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት/ መዝ 118፥24/
ይህች ታላቅ ዕለት  ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ ለቅዱሳን አርድእትና ለቅዱሳት ሴቶች የተገለጠባት ዕለት ናት፡፡    እነዚህ ሁሉ በጸሎት ተግተው በሚጸልዩበት ወራት መንፈስ ቅዱስ  በተከፋፈሉ የእሳት ልሳን አምሳል የወረደበት ቅዱስ ቀን ነው፡፡

አስቀድሞ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ደብረ ዘይት በተባለ ታላቅ ተራራ ላይ ሳሉ እንዲህ ብሎ አስተምሯቸው ነበር “ኀይልን ከላይ ከአርያም እስክልክላችሁ ድረስ በኢየሩሳሌም በጸሎት ቆዩ፡፡”/ሉቃ 24፡36/ መቶ ሃያው ቤተሰብም በኢየሩሳሌም ሀገር በምትገኝ በቤተ መቅደስ በአንድነት ሆነው በጸሎት በመትጋት ቆዩ፡፡ ልጆችዬ መቶ ሃያው ቤተሰብ የሚባሉት 12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእት/አገልጋዮች/ እና 36ቱ ቅዱሳን አንስት/ሴቶች/ ናቸው፡፡

ከዕርገት በኋላ በአሥረኛው ቀን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያት ወዳሉበት፣ በጸሎትና በምሥጋና ወደ ሚተጉበት ሥፍራ በእሳት አምሳል /ምሳሌ/ ወርዶ በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው፡፡ ይሄንንም  ሁኔታ ተከትሎ  ምስጢር ተገለጠላቸው፣ ይፈሩ የነበሩት ሐዋርያትም ወንጌልን ለማስተማር ደፋሮች ሆኑ፣ በተለያየ ቋንቋዎች እንዲናገሩ እውቀት ተሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ይህንን ታላቅ ኀይል እና ሰማያዊ ስጦታን የሰጣቸውን እግዚአብሔርን በታላቅ ዝማሬና እልልታ አመሰገኑት፡፡

Saturday, June 15, 2013

ዕርገተ ክርስቶስ


በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ
“አልቦ ዘዐርገ ውስተ ሰማይ ዘእንበለ ዘወረደ እምሰማይ ወልደ እጓለመሕያው” ዮሐ.3፥13

Ereget

ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡ እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው፡፡ ይህ ኃይለ ቃል ክብር ምስጋና ይግባውና ስለጌታችን፣ አምላካችን፣ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት መውረድ ከድንግል ማርያም መወለድ እና የሰውነቱን ሥራ ጨርሶ በክብር ወደ ሰማይ ማረጉን የሚገልጽ ነው፡፡ እንደሚታወቀው አምላካችን ስለሁለት አቢይ ጉዳዮች ሰው ሆኗል፡፡
  1. ለቤዛነት /ዓለምን ለማዳን/
  2. ለአርአያነት /ምሳሌነት/
የሰውን ልጅ በመውደዱ ልዑል ባሕርዩን ዝቅ አድርጎ ከሰማይ ወረደ ሥጋ ለበሰ በምድር ላይ ተመላለሰ፤ ምድርን በኪደተ እግሩ ቀደሰ፤ ድውያንን ፈወሰ፤ ፍጹም ሰው እንደ መሆኑ ተራበ ፍጹም አምላክ መሆኑንም ያስረዳ ዘንድ አምስት ገበያ ሕዝብ በአምስት እንጀራ በሁለት ዓሣ አጠገበ ማቴ.14፥19 ለእኛ አርአያና ምሳሌ ለመሆን ዝቅ ብሎ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ ዮሐ.13፥14 እኛም ፍለጋውን እንከተል ዘንድ “አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ ለቢፅክሙ” እናንተም ለባልንጀሮቻችሁ እንዲሁ አድርጉ ብሎ አዘዘ፡፡ መምሕረ ትሕትና ነውና በዚህ ዓይነት መልኩ ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር በዚህ ዓለም ኖረ ለሐዋርያት ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን አስተማራቸው ትምህርት በሚገባ ከተረዳለት በኋላ ለድኅነተ ዓለም በማዕከለ ምድር በቀራንዮ ተሰቀለ፡፡