Sunday, September 7, 2014

ለውጥ በሌለው ሕይወት አቆጣጠር - ዛሬ ስንት ዓመተ ምሕረት ነው ?



Dn Melaku ezezew
አንድ ሶርያዊ ክርስቲያን የሚከተለውን ደብዳቤ 1983 . ጽፎ ነበር፡፡ ደብዳቤው እንዲህ ይነበባል፡-
«እስከ 1970 . (የተወለደው 1943 . ነው) «በቤተ ክርስቲያን ትምህርት መሠረት ሥጋ ወደሙ እቀበል ነበር፣ አሥራት አወጣ ነበር፣ ገዳማትን ለመርዳት የተቋቋመ ማኅበር አባል ሆኜ ሌት ተቀን እሠራ ነበር፣ ሁል ጊዜ በመንፈሳዊ ሕይወቴ ውስጥ የመለወጥ ስሜት ነበረኝ፣ ለመማር፣ ለመጾምና ለመጸለይ የነበረኝን ትጋት አስታውሰዋለሁ፡፡ ይሁን እንጂ 1970 . መንፈሳዊ ሕይወቴ ባለበት ቆመ፡፡ እንኳን ከበፊት የተሻለ ምግባር ልፈጽም የነበረኝንም እየተውኩት መጣሁ፡፡ ድካምና መሰልቸት ሕይወቴን ተጫጫነው፡፡ ራዕይ አጣሁ፡፡ ከፊት ለፊቴ ምንም ነገር አይታየኝም፡፡ ግድግዳ ያለ ይመስለኛል፡፡ ቤተክርስቲያን በበለጠ ለማገልገል የነበረኝ ጉጉት ሁሉ ሞተ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በማንኛውም ደብዳቤ ዓመተ ምሕረቱን 1970 እያልኩ እጽፋለሁ፡፡ እስከ አሁን ድረስ (1983 . ማለቴ ነው) በኔ አቆጣጠር 1970 . ነው፡፡ ምክንያቱም ከዚያ በኋላ በኑሮዬ ውስጥ ምንም የተለወጠ፣ ያደገ ወይም የተስተካከለ ነገር የለምና፡፡ ብፁዕ አባታችን፡- እባክዎ ምክርዎን በመለገስ ወደ 1971 . ያሸጋግሩኝ

ሕይወት ካልተለወጠ፣ ካላደገ፣ ሃይማኖት ካልሰፋ፣ ምግባር ካልጸና ትናንት ያሸነፉንን ኃጢአቶች ዛሬ ካላሸነፍን፣ የደከመውን አበርትተን፣ የተሰበረውንካልጠገንን፣ ዘመን ተለውጦ ዘመን ቢተካም፣ የምድርን ዕድሜ እንቆጥራለንን እንጂ እኛ እንደሆንን እንደቆምን ነን፡፡ አንዳንዶቻችን ያኔ ሕጻን ሆነን ሥጋ ወደሙ እንደተቀበልን፣ ሌሎቻችንበወጣትነት ለሰንበት /ቤትና ለጽዋ መርሐ ግብር በነበረን ትጋት ላይ ሌሎችም በማስተማር፣ ቤተክርስቲያንን በማሰራት፣በማስቀደስ በመጸለይና በመጾም፣ በነበረን የጥንት ምግባር አንዳንዶችም ወደ ምንኩስና (ምናኔ) ሲገቡ በነበራቸው የወጣኒነትትጋት እዚያው ላይ ዓመተ ምሕረታችን ቆሟል፡፡

አዲስ አበባ አራት ኪሎ መሐል የአርበኞች ኃውልት አለ፡፡ እዚያ ኃውልት ጫፍ ላይ ሰዓት ተሰቅሏል፡፡ ሰዓቱ የሚያመለክተው አርበኞች አዲስ አበባ የገቡበትን ሰዓት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ቆሟል፡፡ የዛሬው ትውልድ ያንን ሰዓት ሲያየው ጀግኖች አባቶቹ ጠላትን ድል አድርገው ሀገሪቱን ነጻ ያወጡበትን ጊዜ ያስብበታል፡፡ ሰዓት የጥንቲቱን ተግባር ብቻ እያመለከተ ቆሟል፡፡ የዛሬውን ትውልድ ጀግንነትና ዝና የሚያሳይ ሰዓት ግን የለም፡፡ የብዙዎቻችን ሰዓት ቆሟል፡፡ በአንድ ወቅት የሠራነውን መልካም ስራ፣ የነበረን መንፈሳዊ ትጋት፣ የሃይማኖት ጥንካሬና ሰማይ ጥግ የደረሰ ዝና እያመለከተ ቆሟል፡፡ ዛሬ በአቡሻህር አቆጣጠር 2007 . ነው:: በእኛ አቆጣጠርስ ስንት ነው; ሶርያዊ ክርስቲያን «በኔ አቆጣጠር 1970 . ነው» ብሏል፡፡ እርሱ የነበረበትን ዘመን ግን እስከ 1983 . ነበር፡፡


የዘመን መለወጫን በዓል አከበርነውም አላከበርነውም ዘመኑ መለወጡ አይቀሬ ነው፡፡ እያንዳንዷን ቀን ተጠቀምንም አልተጠቀምንም ጊዜው መሮጡ አይቀርም፡፡ እርሱ የራሱን ጊዜ ይቆጥራል፡፡ ይለወጣል፡፡ እኛስ; እስቲ ጊዜ ሰጥተን ራሳችንን እንመርምረው፡፡ በሃይማኖት እየጸኑ፣ በምግባር እየበረቱ፣ በትጋት እየጨመሩ፣ በመንፈሳዊ እውቀት እያበሩ፣ ሰማዕትነትን ይበልጥ እያፈኩ ካልሄዱ ዘመኑ ብቻውን ቢቀየር «እንኳን አደረሳችሁ».ያስብላልን; የአክሱምንም አደባባይ የጎበኘ ሰው ሦስት ነገሮችን መታዘብ ይችላል፡፡ ተጠርቦ ተቀርጾ ሃውልት የሆነ ድንጋይ አለ፡፡ ሃውልት ለመሆን ተጠርቦ ቅርጽ ሳይወጣለት ልሙጥ ሆኖ የቀረ አለ፡፡ ለሀውልትነት ተመርጦ ሳይጠረብ ሳይቀረጽ የቀረ አለ፡፡ በመንፈሳዊ ጉዞም እነዚህ ሦስቱ ነገሮች ሊያጋጥሙ ይችላሉ፡፡ ለሰማያዊ ዋጋ ተመርጠው በብዙ ፈተና ተጠርበውና ተቀርጸው ጉዞአቸውን የፈጸሙ አሉ፡፡ ተመርጠው ተጠርበው ግን ገና ቅርጽ መያዝ ሲቀራቸው ባሉበት የቀሩ አሉ፡፡ በሌላ በኩል ተመርጠው ከመጡ በኋላ ከዚያ ያለፈ ተግባር ላይ ያልዋሉም አሉ፡፡ የእነዚህ የሦስቱም የዘመን አቆጣጠራቸው ይለያያል፡፡ አንዱ በደረሰበት . ሌሎቹ አልደረሱምና፡፡

በወንጌል ታሪኩ የተጠቀሰው የጠፋው ልጅ አባት ልጁ ከጠፋበት ሀገር ሲመለስ «ይህ ልጄ ሞቶ ነበር ህያው ሆኗል».ብሎ ነበር የተናገረው፡፡ ልጅ እኮ ይንቀሳቀሳል፣ ይበላል፣ ይጠጣል ግን ሞቷል ተባለ ለምን; የሱ የዘመን አቆጣጠር ከአባቱ ቤት ሲጠፋ መቁጠሩን አቁሞ ነበርና፡፡ በመንፈሳዊ ጉዞ የነበረው ለውጥ ስላቆመ ሞተ ተባለ፡፡ ትልቁ ጥያቄ ማን ተለወጠ ነው፡፡ ዘመን ተለወጠ; ሰው ተለወጠ; ወይስ ሁለቱም ተለወጡ; ዘመን ይለወጣል፡፡ አይቀሬ ነው፡፡ የስነ ፍጥረት ስርዓት ሁሉ የእግዚአብሔርን ህግ ሳያፋልስ ይኖራልና፡፡ አስቸጋሪው ነገር እርሱ አይደለም፡፡ እስከ ዘመነ ምጽዓት ዘመን ይመጣል፣ ያልፋል፣ በሌላ ይተካል፡፡ ሰው ተለወጠ; ለሚለው ጥያቄ መልስ ማግኘት ግን ከባድ ነው፡፡ ይህን ጥያቄ ከባድ ያደረገው በሰው ኑሮ ውስጥ ሦስት ዓይነት ለውጥ ስላለ ነው፡፡ በመንፈስ መለወጥ፣


በአካል መለወጥ፣ በባሕላዊም ይሁን በዘመናዊ መንገድ በሚገኝ እውቀት የሰው እውቀት ይለወጣል፣ ያድጋል፣ ይሰፋል፣ ይጎለምሳል፡፡ ወደደም ጠላም የሰው አካል የተፈጥሮውን ሂደት ጠብቆ ይለወጣል፣ ጽንሱ ይወለዳል፣ ሕጻኑ ያድጋል ወጣት ይሆናል፣ ወጣቱ ይጎለምሳል፣ ጎልማሳው ያረጃል፣ አካላዊ ጸባዩም በዚያው ልክ ይለወጣል፡፡ ትልቁ ፈተና መንፈሳዊ ለውጡስ የሚለው ላይ ሲደርስ ነው፡፡ መንፈሳዊ ለውጥ ከነዚህ ከሁለቱ ለውጦች የተለየ ነው፡፡ ተጋድሎ ከሥጋና ደም ጋር አይደለምና፡፡ የሰውየውን ታላቅ ጥረት፣ ሰማዕትነት እና የሃይማኖትን ጽናት የግድ ይላል፡፡ በዚህም የተነሳ በእውቀት ጎልምሰው፣ በዕድሜ አርጅተው፣ በመንፈሳዊ ለውጥ ግን ገና ሕጻናት የሆኑ ወይም ደግሞ በሕጸንነት እድሜ ላይ የጊዜ መቁጠሪያ ሰዓታቸውን ያቆሙ ብዙ ናቸው፡፡ ሌላው ቀርቶ ስለ መንፈሳዊ ሕይወትና ስለ ሃይማኖት እጅግ ብዙ የተማሩ በእውቀት ለሌሎች ሊተርፉ የሚችሉ ሌሎችን አስተምረው ለፍሬ ያበቁ ሰዎች በመንፈሳዊ ሕይወት ለውጣቸው ገና ወጣኒያን ሆነው የሚገኙበት አጋጣሚ አለ፡፡ ስለዚህም ሌላ የዘመን መለወጫ ከማክበራችን. አዲስ አመት ገባ እያልን ዶሮና በግ ከማረዳችን. እንደ ምዕራባውያውኑ ወደ ኋላሩ (Count down) ከመቁጠራችን በፊት ለቀጣዩ ጥያቄ መልስ እንፈልግ፡፡

ለውጥ በሌለው ሕይወት አቆጣጠር - ዛሬ ስንት ዓመተ ምሕረት ነው ?
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
www.melakuezezew.info - ስንክሳር ድረገጽ

Monday, August 18, 2014

አመታዊ የቅድስት ኪዳነ ምሕረት በዓል


እንኳን ለቅድስት ኪዳነ ምሕረት አመታዊ በዓል አደረሰን
“ወዳጄ ሆይ ተነሺ፣ ውበቴ ሆይ ነይ”
መኃ 2፡10

Sunday, August 3, 2014

ፍልሰታ ለማርያም

ፍልሰታ ለማርያም
(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐምሌ ፳፯ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ተዋዳጆች ሆይ! ዛሬ የምንማማረው በእንተ ፍልሰታ ለማርያም አይደለም፡፡ ስለ ራሳችን ፍልሰታ እንጂ፡፡ ኹላችንም ስለ እመቤታችን ፍልሰታ የመናገር ችግር የለብንም፡፡ ዛሬ እንድንማማርና እንድንወቃቀስ የፈለግኹት በሕይወታችን ከግብርናተ ዲያብሎስ ወደ ክርስቶስ ሳንፈልስ (ሳንሻገር) የእመቤታችንን ፍልሰታ ብቻ ለምናከብር ለየኔ ቢጤዎች ነው፡፡


እስኪ ከኹሉም አስቀድመን ለራሳችን ይኽን ጥያቄ እንጠይቀው፡፡ “በሕይወት ዘመኔ ስንት የፍልሰታ አፅዋማት አለፉ? እኔስ በዚኹ ጉዳይ ስንት ጊዜ ተናገርኩ? ስለዚኹ በዓል ለማወቅ መጓጓቴ ለማያውቁትም የማውቀውን ያኽል መናገሬ ክፋት ባይኖረውም እኔ ራሴስ ምን ለውጥ አመጣኁ? ምን ፍሬ አፈራኁ? ስለ ፍልሰታ እየተናገርኩ እኔ ራሴ ሳልፈልስ ስንት ዘመናት አለፉ? ከአገልግሎቴ ምን ረብሕ አገኛችኁ?”

ተወዳጆች ሆይ! እውነት ነው ምንም ሳንለወጥ ብዙ ዘመናትን አሳልፈናል፡፡ እኛ በሕይወት ሳንሻገር ብዙ የመሻገር (የፋሲካ) በዓላትን አክብረናል፡፡ እኛ ሳንነሣ ብዙ የመነሣት (የትንሣኤ) በዓላትን አክብረናል፡፡ እኛ በሕይወት ሳንፈልስ ብዙ የፍልሰታ በዓላትን አክብረናል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለእንደዚኹ ዓይነት ምልልሳችን እንዲኽ ነው የሚለን፡- “ቀንንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችኁ፡፡ ምናልባት በከንቱ ለእናንተ ደክሜአለኹ ብዬ እፈራችኋለኹ” /ገላ.፬፡፲-፲፩/፡፡ በዓላትን የምናከብራቸው ቀናትን፣ ወራትን፣ ወይም ዘመናትን ለማክበር አይደለም፡፡ እነዚኽን በዓላት ምክንያት አድርገን ራሳችንን የበለጠ ወደ እግዚአብሔር ለማቅረብ ነው፡፡ እነዚኽን በዓላት ምክንያት አድርገን የእግዚአብሔር ቸርነቱን ለእኛም ያለውን ፍቅሩን ተረድተን እንድናመሰግነው ነው፡፡ ፍልሰታ ለማርያምን የምናከብረው በእመቤታችን ላይ የምንጨምረው ነገር ስላለ አይደለም፡፡ ፍልሰታን የምናከብረው እንደ እመቤታችን እንኳን ባይኾን የዓቅማችንን ያኽል በዚኽ ጊዜአዊ መቆያችን እስካለን ድረስ በንጽሕና በቅድስና ከምንም በላይ ደግሞ እግዚአብሔርን በፊደላት ሳይኾን በሕይወታችን ዐውቀነው አጣጥመነው የምንኖር ከኾነ ትንሣኤ፤ ፍልሰት እንዳለን እንድናውቅ ነው፡፡
ይኽን ግምት ውስጥ ባላስገባ መንገድ የምናከብረው ከኾነ ግን የእስከ አኹኑ ምልልሳችን አይሁዳዊ ምልልስ ነበር ማለት ነው፡፡ እንዴት? አይሁዳውያን ሕገ ኦሪትን የተሰጠቻቸው ኃጢአታቸውን በርሷ መስታወትነት ዐይተው ንስሐ እንዲገቡባት ስትሰጣቸው፥ እነርሱ ግን የንስሐ ፍሬ ሳያፈሩባት እንዲኹ ስለተመኩባት ለሕይወት የተሰጠቻቸው ሕግ ሞት ኾና አግኝቷታልና፡፡ እኛም እንዲኽ ለኵነኔ ያይደለ ለጽድቅ የተሰጠችን ወንጌል ፍሬ የማናፈራበት ከኾነ ክርስቶስን ከማያውቁ አይሁዳውያን የባስን ነን፡፡

እስኪ አንድ ምሳሌ አንሥተን እንማማር፡፡ አንድ የእግር ኳስ ክለብ በየጊዜው ተጋጣሚውን እንደምን ማሸነፍ እንዳለበት ልምምድ የሚያደርግ ከኾነ ክኅሎቱ ይዳብራል፡፡ ተጋጣሚውንም በቀላሉ ማሸነፍ ይቻሏል፡፡ በአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች የሚጫወቱ ክለቦች በየአገሩ እየዞሩ አቋማቸውን እየለኩ ያሉት በቀጣዩ ዓመት ለዋንጫ የሚያበቃቸውን ውጤት ለማምጣት እንጂ ተጨዋቾቹ ዕረፍት ማድረግ ስላልፈለጉ አይደለም፡፡ እኛስ! ፍልሰታን የምናከብረው ለምንድነው? እንደ እመቤታችን መነሣት እንዳለ እንድናውቅ ያንንም ሕይወት ገንዘብ ለማድረግ ወይስ እንዲኹ ልማድ ስለኾነብን? ለምንድነው የምንጦመው? ይኽ ጥያቄአችን ወደ ቀጣዩ መፍትሔ ያመራናል!!!

ክርስትና ጠቅላላ ዕውቀት አይደለም፤ እኛ በክርስቶስ ክርስቶስም በእኛ ኾኖ እግዚአብሔርን ማምለክ ነው እንጂ፡፡
እግዚአብሔርን ማምለክ ሲባልም በንግሥ በዓላት ላይ መሳተፍ፣ መዝሙር ወይም ማኅሌት ወይም ሰዓታት ላይ መሳተፍ፣ መጸለይ፣ መጦም፣ አስራት በኵራትን ማውጣት አይደለም፡፡ እነዚኽ ኹሉ ከእውነተኛ አምልኮአችን በኋላ የሚከተሉ ናቸው፡፡ ስለዚኽ እውነተኛ አምልኮ ከዚኽ የሚያልፍ (ከፍ የሚል) ነው፡፡ እውነተኛ አምልኮ እግዚአብሔር እኛን ምን ያኽል እንደሚያፈቅረን ማወቅ ነው፡፡
አዳም በኤደን ገነት ውስጥ ሳለ እግዚአብሔርን ያውቀው ነበር፤ መፍቀሬ ሰብእ እንደኾነ፡፡ በበደለ ጊዜ ግን ዓይነ ልቡናው ታወረ፡፡ እግዚአብሔር ስለ ፍቅሩ አዳምን ሲፈልገው ሲሸሽ የነበረውም በዚኹ ምክንያት ነው፡፡ ድምጹን እንኳን መስማት የተሳነው የእግዚአብሔርን ፍቅር አልረዳ ብሎ ነው /ዘፍ.፫፡፲/፡፡ እግዚአብሔር ግን በባሕርዩ ፍቅር ነውና ሰዎች ፍቅሩን እንረዳለት ዘንድ ይሻል፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችንን በሙሉ ስናነብ የምንገነዘበው ነገር ቢኖር እግዚአብሔር ምን ያኽል የሰው ፍቅርን እንደተጠማ ነው፡፡ እግዚአብሔር አንድ አብርሃምን ሲፈልግ የነበረው፣ በቤቱ ውስጥ ገብቶ ማዕድን ሲበላ የነበረው፣ ከነ ይሥሐቅ ጋር የተወዳጀው፣ ከእነ ያዕቆብ ጋር ሲታገል ያደረው፣ ከእኔ ሙሴ ጋር በሲና ተራራ ፵ ቀንና ሌሊት ሲጨዋወት የነበረው ፍቅሩን የሚረዳለትና የሚያውቅለትን ሰው ፍለጋ ነው፡፡
እስራኤላውያን ፍቅሩን ይረዱለት ዘንድ ሕጉን በሙሴ በኵል ሰጣቸው፡፡ ሕጉም ገና ሲዠምር፡- “አነ ውእቱ እግዚአብሔር ዘአውፃእኩከ እምድረ ግብጽ እምቤተ ቅንየት - ጽኑ አገዛዝ ከምትገዛበት ከግብጽ አገር ያወጣኹኅ ፈጥሬ የምገዛኅ እግዚአብሔር እኔ ነኝ” ነው የሚለው /ዘጸ.20፡2/፡፡ እግዚአብሔር ከእኛ የሚሻው ተቀዳሚ ነገር ርሱን እንድናውቀው ነው ማለት ነው፡፡ ስናውቀው ፍቅሩን እንረዳለታለን፤ ደግሞም እንወዷለን፡፡ በነቢዩ ሆሴዕ አድሮ የተናገረውም ቢኾን፡- “ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን ከሚቃጠልም መሥዋዕት ይልቅ እግዚአብሔርን ማወቅ እወድዳለኹና” ነው የሚለው /ሆሴ.፮፡፮/፡፡ አስቀድመን እንደተናገርን ከመስገዳችን በፊት፣ ከመጦማችን በፊት፣ ከመጸለያችን በፊት፣ ሰዓታት ከመቆማችን በፊት፣ ሱባዔ ከመግባታችን በፊት እግዚአብሔር እንድናውቀው ይፈልጋል፡፡
ክብር ይግባውና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚኽ ምድር የመጣውም ለሌላ ዓላማ አይደለም፤ የሰው ፍቅር ጠምቶት እንጂ /ዮሐ.፬፡፯/፡፡ ጌታችን ከኀጢአት በቀር የእኛን ባሕርይ የተዋሐደው እኛ ከርሱ ጋራ እንድንዋሐድ ነው፡፡ የሰውነቱ ሕዋሳት ሲያደርገንም የአብ ፍቅሩ እንደምን ጥልቅ እንደኾነች እንድንረዳ ነው፡፡ አብ አንድያ ልጁን እስኪሰጠን ድረስ እንደወደደን እንድናውቅ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ በበዓለ ኃምሳ የተሰጠን ፍቅሩን ተረድተንለት በፍቅሩ ኖረን በእውነት ወዳጃችን እንደኾነ ዐውቀን በሕይወት እንድንኖርለት ነው፡፡ ልጅነትን አግኝተን በወይን ክርስቶስ ውስጥ ቅርንጫፍ የኾንነው የወልድን የባሕርይ ልጅነት በጸጋ ተካፋይ እንድንኾን ነው፡፡ አባ አባት ብለን እንጠራው ዘንድ የልጅነትን ሥልጣን የሰጠን ስለዚኹ ነው፡፡ በዚኽም ማንም ፍጥረት ሊደርስበት የማይችል የአባትነት ፍቅሩን እንድንረዳ ነው፡፡
በቅዱስ ቁርባን ክርስቶስ በእኛ እኛም በክርስቶስ ነው የምንኾነው፡፡ ከዚኽም የተነሣ አብን እናውቋለን፡፡ ምክንያቱም ከወልድ በቀር አብን የሚያውቀው ስለሌለ /ማቴ.፲፩፡፳፮/ ወልድ ደግሞ በለበሰው ሥጋ ከእኛ ጋራ ስለተዛመደና እኛም ከርሱ ጋራ ስለተዛመድን በርሱ በኩል እግዚአብሔር አብን እናውቋለን፡፡ ገና ስንዠምር እውነተኛ አምልኮ ያለውነውም በዚኹ ተፈጻሚነቱን ያገኛል፡፡
የሰው ልጆች አጥተነው የነበረው እውነተኛ ሥርዓተ አምልኮታችን በክርስቶስ (በቅዱስ ቁርባን) በኵል ተመልሶልናል፡፡ አስቀድመን እንደተናገርን ቀዳማዊ አዳም እግዚአብሔርን ከማወቅ ርቆ መታዘዝን እምቢ ብሎ ነበር፡፡ ክርስቶስ ግን ለአባቱ በመታዘዝ እውነተኛ አምልኮአችንን መልሶልናል፡፡
ርግጥ ነው በቅዱሳት መጻሕፍት እግዚአብሔርን እናውቋለን፡፡ በቅዱስ ቁርባን ግን በልጁ ደም ከርሱ ጋር እንታረቃለን፤ ርሱ በእኛ እኛም በርሱ እንኾናለንና ከየትኛውም መንገድ በላይ እናውቋለን፡፡ የኤማሁስ መንገደኞችን እናስታውሳቸው! የኤማሁስ መንገደኞች ጌታችን ከሙሴ እስከ ነቢያት ያሉ መጻሕፍትን ሲነግራቸው ልባቸው ይቃጠልባቸው ነበር፡፡ ከነርሱ ጋር እራት በበላ ጊዜ ግን ዓይኖቻቸው ተከፈተ፤ ክርስቶስንም ዐወቁት /ሉቃ.፳፬፡፴፪/፡፡
ታድያ እኛ እግዚአብሔርን በእውነት እያመለክነው ነው ወይ? በሌላ አገላለጥ ክርስቶስ በእኛ እኛም በክርስቶስ ውስጥ አለን ወይ? አብን ማወቅ የምንችለው የክርስቶስ ሕዋሳት የኾንን እንደኾነ ብቻ ነው፤ ወልድን የምናውቀው ብልቶቹ እንደኾንን ብቻ ነው፤ መንፈስ ቅዱስንም እንደዚኹ፡፡ ታድያ እግዚአብሔርን የምናወቀው በፊደላት ነው፥ ወይስ በእውነት በክርስቶስ ውስጥ ኾነን ማለትም ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በመቀበል? በዚኽ ፍልሰታ ምን አስበናል አኹንም እንደ አምና እንዲኹ በዘልማድ ለማክበር? እንዲኽስ ከቶ አይኹን!!! እስኪ ከንስሐ አባቶቻችን ጋር እንማከርና ፍልሰታን በእውነት ፍልሰታ ለማርያም ብቻ ሳይኾን ለእኛም እናድርገው፡፡ ይኽን እንድናደርግ የእግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን አማላጅነት የቅዱሳን መላዕክት ተራዳኢነት ይርዳን አሜን!!!

Monday, July 21, 2014

“ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ፤ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ፤ ስለ መንግሥተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ፡፡” ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ ቁ.6

ሶሪያዊው ቅዱስ ኤፍሬም በቅዱስ ዳዊት ሕይወት የተከወናውን በምሥጢር ስቦ አምጥቶ የሰማዕታትን ክብር አጎልቶ ተናግሮበታል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊትን እግዚአብሔር አምላክ ለእስራኤል አነገሠው፡፡ በዙሪያው የነበሩ ኤሎፍላዊያንን አጥፍቶ ደብረ ጽዮንን /መናገሻ ከተማውን/ አቅንቶ ሲኖር ከዕለታት አንድ ቀን ዳዊት ታመመ፡፡የዳዊትን መታመም ሰምተው፣ ካሉበት ተነስተው የዳዊትን ከተማ በተለይም ቤተልሔምን ከበቧት፡፡ ዳዊት ይህን ሰምቶ “ወይ እኔ ዳዊት! ድሮ ታመምሁና ጠላቶቼ ሰለጠኑ ሲል የኀያላኑን ልቦና ለመፈተን ከቤተልሔም ምንጭ ውኃ ማን ባመጣልኝ?” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የጭፍሮቹ አለቆች ሦስቱ ማለትም አዲኖን፣ ኢያቡስቴ ኤልያና ረዋታቸውን /የውኃ መያዣ/ ይዘው፣ ጦራቸውን አሰልፈው፣ ጠላቶቹን ድል ነስተው፣ ዳዊት ሊጠጣ የወደደውን ውኃ አመጡለት፡፡ቅዱስ ዳዊትም ያንን ውኃ አፈሰሰው “ለምን አፈሰስከው?” ቢሉት “ደማችሁን መጣጠት አይደለምን?” ብሎ፤ ይህም ከጽድቅ ገብቶ ተቆጠረለት፡፡ 2ሳሙ.23፥13-17

አባቶቻችን ይህንን ሲያመሰጥሩት የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ አባታችን አዳም ከተድላ ገነት ወደ ምድረ ፋይድ፥ ከነጻነት ወደ መገዛት፥ ከልጅነት ወደ ባርነት፥ በወረደና ፍትወታት እኩያት ኀጣውእ በጠላትነት በተነሱበት ጊዜ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከተገኘ ከጌታ ጎን የተገኘ ማየ ገቦ ይጠጣ ዘንድ ወደደ፡፡ የትሩፋት አበጋዞች ሃይማኖት፣ ተስፋ፣ ፍቅር፣ ፈጥነው ተነሱ፡፡ በአጋንንት ከተማ ተዋጉለት ይጠጣው ዘንድ የወደደውን ማየ ገቦ አመጡለት፡፡ ማለትም የአዳም ልጅነት በከበረው የክርስቶስ የደሙ ፈሳሽነት የሥጋው መሥዋዕትነት ተመለሰለት፡፡ ይህንን ለአዳምና ለልጆቹ የባህርይ አምላክ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ እያሰቡ ሰማዕታት በእግዚአብሔር ፍቅር ተቃጥለው “እግዚአብሔርን ካዱ ለጣዖት ሰገዱ” ሲባሉ “እግዚአብሔርን አንክድም ለጣዖት አንሰግድም” ብለው ደማቸውን አፈሰሱ ይህም ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፡፡ /ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ ዘሐሙስ/

“ሰማዕት” ማለት ምስክር ማለት ነው፡፡ ይህ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ብሎ ማፍሰስ ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፥ የዳዊት ወታደሮች ስለ ዳዊት ፍቅር ብለው “ደማችን ይፍሰስ” እንዲሉ፤ ዳዊትም ያመጡለትን ውኃ መጠጣት ደማችሁን እንደመጠጣት ነው ብሎ በፍቅር ምክንያት ውኃውን እንዳፈሰሰው፥ ይህም ጽድቅ ሆኖ እንደተቆጠረለት፥ የእግዚአብሔር ወዳጆች የሆኑ ቅዱሳን ሰማዕታትም እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር ሃይማኖት የሆነችው እውነተኛይቱን ሃይማኖት ወደው ደማቸውን አፈሰሱ፣ አጥንታቸውን ከሰከሱ፣ ስለዚህ እንደ ፀሐይ አብርተው በሰማያት ዛሬም ስለ እኛ እየማለዱ አሉ፡፡

ከእነዚህም መካከል ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስባቸዋለች፡፡ ሐምሌ 5 ሰማእትነት የተቀበሉበት ቀን መታሰቢያቸውን ታዘክራለች፡፡ ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘርኀ ሐምሌ ዕለቱን በማስመለከት ያገኘነውን መረጃ እንዲህ ተዘጋጅቷል፡፡

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ አምስት በዚች ቀን የክቡራንና የዐበይት አባቶቻችን ሐዋርያት የጴጥሮስና የጳውሎስ የሰማዕትነታቸው መታሰቢያ ነው፡፡ ሰላም ለከ ጴጥሮስ ተልሚድ፡፡ ዘኢያቅበጽከ ተስፋ ነገረ ኑፋቄ ወካህድ፡፡ እንዘ ትረውጽ ጥቡዐ ለመልእክተ ክርስቶስ ወልድ፡፡ አመ ለሊከ ወሬዛ ቀነትከ በእድ፡፡ ወአመ ልህቀ አቅነትከ ባዕድ፡፡

ይህም ጴጥሮስ ከቤተ ሳይዳ ነበር ዓሣ አጥማጅም ነበር ጌታችንም ከተጠመቀባት ዕለት ማግሥት አግኝቶ መረጠው፤ ከእርሱ አስቀድሞም ወንድሙ እንድርያስን አግኝቶ መረጠው፡፡ መድኃኒታችንንም እስከ መከራው ጊዜ ሲአገለግለው ኖረ፤ ፍጹም ሃይማኖት፣ ለጌታውም ቅንዓትና ፍቅር ነበረው፡፡ ስለዚህም በሐዋርያት ሁሉ ላይ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡

ጌታችንም ሰዎች ማን እንደሆነ ማንም እንደሚሉት ስለ ራሱ በጠየቃቸው ጊዜ ሌሎቹ ኤርምያስ ይሉሃል ወይም ኤልያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይሉሃል አሉት፡፡ ጴጥሮስ ግን የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ አንተ ነህ አለ፡፡ ጌታችንም የሃይማኖት አለት የቤተ ክርስቲያንም መሠረት ነህ ብሎ ብፅዕና ሰጠው የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻ ቁልፍ ሰጥቼሃለሁ አለው፡፡

አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስንም ጸጋ ከተቀበለ በኋላ ተናጋሪዎች በሆኑ በዚህ ዓለም ተኲላዎች መካከል ገባ በውስጣቸውም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰበከ፤ ቊጥር የሌላቸው ብዙዎች አሕዛብንም መልሶ የዋሆች ምእመናን አደረጋቸው፡፡

ጌታችንም የማይቈጠሩ ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችን በእጆቹ አደረገ፤ ጥቅም ያላቸው ሦስት መልእክቶችንም ጽፎ ለምእመናን ላካቸው፡፡ ለማርቆስም ወንጌሉን ተርጒሞ አጽፎታል፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ፤ የከተማው መኳንንት ወደሚሰበሰቡበት ወደ ታላቁ የጨዋታ ቦታም ሔዶ በታላቅ ድምፅ እንዲህ ብሎ ተናገረ የሚራሩ ብፁዓን ናቸው ለርሳቸውም ይራሩላቸዋልና የዚህንም ተከታታይ ቃሎች ተናገረ፡፡ ከዚያም ከዚያ የነበሩ አራት የደንጊያ ምሰሶዎችም በሚያስፈራ ድምፅ አሜን አሉ፤ የተሰበሰቡትም ይህን ቃል በሰሙ ጊዜ ደነገጡ፡፡ ከሰባ ዓመት ጀምሮ ሰይጣን ያደረበት አንድ ሰው ነበረ፤ ከእነዚያ ደንጋዮች ቃልን ስለ ሰማ ያን ጊዜ ጋኔኑ ጣለው ከእርሱም ወጥቶ ሔደ፡፡ መኳንንቱም ፈርተዋልና ስለዚህ ነገር እያደነቁ ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡

ከከተማ መኳንንቶችም ቀውስጦስ የሚባል አንዱ ወደ ቤቱ በገባ ጊዜ ስሟ አክሮስያ ለምትባል ሚስቱ ዓለምን ስለ መተው ለድኆችም ስለመራራትና የመሳሰለውን ቃል ጴጠሮስ እንዴት እንዳስተማረ ነገራት፡፡ እርሷም በሰማች ጊዜ በልቧ ነቅታ ይህ ነገር መልካምና ድንቅ ነው አለች፡፡ ጴጥሮስ ያስተማረውንም ሁሉ ያደርጉ ዘንድ በአንድነት ተስማሙ ከዚህም በኋላ ገንዘባቸውን ሁሉ ለድኆች ሰጡ ከዕለት ራት በቀር ምንም አላስቀሩም፡፡ ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ንጉሡ ስለ መንግሥት ሥራ ከርሱ ጋራ ለመማከር በቶሎ እንዲደርስ ወደርሱ መልእክትን ላከ፡፡

ቀውስጦስም ይህን በሰማ ጊዜ ገንዘብ ስላልነበረው ፈርቶ ደነገጠ ተጨነቀም፡፡ ምክንያትም አመካኝቶ ይሠወር ዘንድ ከሚስቱ ጋራ ተማከረ፡፡ እርሷ ግን ምክንያት አታድርግ ነገር ግን ወደ ንጉሡ ሒድ የጴጥሮስም አምላክ ጐዳናህን ያቅናልህ አለችው፤ እርሱም ነገርዋን ተቀብሎ ወደ ንጉሡ ሔደ፤ በመንገድም ከእግዚአብሔር የታዘዘ ብዙ በረከትን አገኘ፡፡ ወደ ንጉሡም ደረሰ፤ ንጉሡም በደስታና በክብር ተቀበለው፡፡

ከሦስት ዓመት በኋላም ወደ ቤቱ በተመለሰ ጊዜ ሁለቱ ልጆቹ የተመረዘ ውኃ ጠጥተው እነሆ ሙተው ነበር፤ ሚስቱም ለእርሱ መንገርን ፈራች ብዙ ምሳሌዎችን ከመሰለችለት በኋላ ነገረችው፡፡ በሰማ ጊዜም እጅግ አዝኖ አለቀሰ፡፡ ሚስቱም እንዲህ አለችው ጌታዬ ሆይ ልባችን የሚጽናናበትን እርሱ ያደርግልናልና የጴጥሮስን ፈጣሪ እግዚአብሔርን እንለምነው፡፡ ሊጸልዩም በጀመሩ ጊዜ ቀውስጦስና አክሮስያ ሆይ የደቀ መዝሙሬ የጴጥሮስን ቃል ስለሰማችሁና ስለተቀበላችሁት ስለዚህ ልጆቻችሁን በሕይወታቸው እሰጣችኋለሁ የሚል ቃልን ከሰማይ ሰሙ ያን ጊዜም ልጆቻቸው ድነው ተነሡ ቀውስጦስና ሚስቱም ደስ አላቸው የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት፡፡

አሊህም ከሞት የተነሡ ልጆች ለቅዱስ ጴጥሮስ ደቀ መዝሙሮቹ ሆኑ፤ የአንዱ ስሙ ቀሌምንጦስ ነው እርሱም ቅዱስ ጴጥሮስ ያየውንና ጌታችን በሥጋ ወደ ሰማይ በሚዐርግ ጊዜ የገለጠለትን ምሥጢር ሁሉ የነገረው ነው፤ ሰዎች ሊያዩአቸው የማይገባቸውን መጻሕፍትን አስረከበው፡፡ ይህንም ቀሌምንጦስን ሊቀ ጵጵስና ወንድሙን ዲቁና ሾማቸው፡ ከዚህም በኋላ ዳግመኛ ቅዱስ ጴጥሮስ አምላክን የወለደች የንጽሕት ድንግል እመቤታችን ማርያም ክብርዋን በምሳሌ አየ፡፡

በቀስት አምሳል ደመናን አይቷልና በላይዋም የብርሃን ድንኳን ነበረ በድንኳኑም ውስጥ አምላክን የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያም ተቀምጣለች፡፡ በእጆቻቸው ውስጥ የነበልባል ጦሮችንና ሰይፎችን የያዙ መላእክትና የመላእክት አለቆች በዙሪያዋ ነበሩ፡፡ እንዲህም እያሉ ያመሰግኗት ነበር ከእርሷ የድኅነት ፍሬ የተገኘ የሠመረች የወይን ተክል አንች ነሽ፡፡ ማሕፀንሽ የእግዚአብሔርን በግ የተሸከመ ንጽሕት አዳራሽ አንቺ ነሽ፡፡

ሁለተኛም እንዲህ ይሏት ነበር፡፡ የብርሃን እናቱ ሆይ የምሕረት መገኛ ሆይ ደስ ይበልሽ የአማልክት አምላክ የፍጥረት ሁሉ ጌታ የሆነ የመድኅን ዙፋን ሆይ ደስ ይበልሽ ክብርና ምሥጋናን የተመላሽ የፍጥረት ሁሉ እመቤት ደስ ይበልሽ፡፡

መላእክትም ምሥጋናዋንና ሰላምታዋን በአደረሱ ጊዜ ክብር ምሥጋና ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእርስዋ ተገልጦ ከእርስዋ በቀር ማንም ሊያውቀው የማይቻል ነገርን ነገራት ወዲያውኑም ምድር ተናወጸች ሊነገር የማይቻል ምሥጢራትንም ገለጠላት፡፡

ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን በሀገሩ ሁሉ ቅዱስ ወንጌልን ይሰብክ ዘንድ ጴጥሮስን አዘዘው፡ ጴጥሮስም ወጥቶ ሔደ፤ ኢዮጴ ወደምትባል የባሕር ዳርቻና ልድያ ወደምትባል አገር ደረሰ፡፡

በአንዲት ዕለትም በኢዮጴ ሳለ ብርህት ደመና ዞረችው፡፡ እነሆም ሰፊ መጋረጃ ወደ እርሱ ወረደች፤ በውሰጥዋም የእንስሳት የምድረበዳ አውሬዎችና የሰማይ አዕዋፍ አምሳል ነበረ፡፡ ጴጥሮስ ሆይ ተነስና አርደህ ብላ የሚል ቃልም ከሰማይ ጠራው፡፡ ጴጥሮስም አቤቱ አይገባኝም ርኩስ ነገር አልበላም ወደ አፌም ከቶ አልገባም አለ፡፡

ያም ቃል ዳግመኛ ጠራውና እግዚአብሔር ንጹሕ ያደረገውን አንተ ርኩስ ነው አትበል አለው፡፡ ያም ቃል ሦስት ጊዜ መላልሶ እንዲህ ነገረው፡፡ በየንግግሩም ወደ እሪያዎች ወደ አራዊትና ወደ አዕዋፍ ስዕሎች ያመለክተው ነበር፤ ከዚህም በኋላ ያቺ መጋረጃ ወደ ሰማይ ተመለሰች፡፡

ጴጥሮስም ስላየው ራዕይ አደነቀ፤ ይህም ራዕይ ወደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር የሚመለሱ አሕዛብን ስለመቀበል እንደሆነ አስተዋለ፤ ለወንሞቹ ሐዋርያትም አሕዛብ የእግዚአብሔርን ቃል እንደተቀበሉ የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስንም ከወገኖቹ ጋር እንዳጠመቀው ነገራቸው፡፡

ከዚህ በኋላም ጴጥሮስ ከዮሐንስ ጋራ ጌታችን እንዳዘዛቸው ወደ አንጾኪያ ከተማ ገቡ፡፡ የአገሪቱንም ሁኔታ ይጠይቅ ዘንድ ጴጥሮስ ዮሐንስን ላከው ሰዎችንም አግኝቶ ክፉ ነገር ተናገሩት፡፡ ሊገድሉትም ፈለጉ፤ እያለቀሰም ተመለሰ፤ ሰውነቱም ተበሳጨች ጴጥሮስንም አለው አባቴ ሆይ የእሊህ ጎስቋሎች ክፋታቸው እንዲህ ከሆነ ወደ ነገሥታቱና ወደ መኳንንቱ ገብተን በጌታችን ስም በሰበክን ጊዜ ምን እንሆን ይሆን እንዴትስ ሃይማኖትን እናስተምራለን፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ወዳጄ ሆይ የሃያውን ቀን መንገድ በአንዲት ሌሊት ያመጣን እርሱ ሥራችንን በአንዲት መልካም ያደርግልናልና አትፍራ፤ አትዘንም አለው፡፡ከዚህም በኋላ ወደ ከተማ መካከል ገብተው ክብር ይግባውና በጌታችን ስም ሰበኩ የከተማው ሰዎችና የጣዖታቱ አገልጋዮችም በእነርሱ ላይ ተሰበሰቡ ታላቅ ድብደባንም ደበደቧቸው፤ አጎሳቆሏቸውም፤ ግማሽ የራስ ጠጉራቸውንም ላጭተው ተዘባበቱባቸው፤ አሥውም በግንብ ውስጥ ጣሏቸው፡፡

ከዘህም በኋላ ተነሥተው ይረዳቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ፤ ወዲያውኑም ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኪሩቤልና ሱራፌል እያጀቡት ተገለጠላቸውና እንዲህ አላቸው፡፡ መረጥኋችሁ ጴጥሮስና ዮሐንስ ሆይ በዘመኑ ሁሉ እኔ ከእናነተ ጋራ እኖራለሁና አትፍሩ፤ አትዘኑም፡፡ ለመዘባበቻም በራሳችሁ መካከል ስለላጩአችሁ አታድንቁ ይህም መመኪያና ክብርን የክህነት ሥርዓትና ምልክትንም ይሆናችኋል፡፡ ካህን የሚሆን ሁሉ ያለዚህ ምልክት ሥጋዬንና ደሜን ማቀበል አይችልም፡፡

ይህ ምልክት እያለው የሚሞት ካህንም ኃጢአቱ ይሠረይለታል፡፡ ይህን ካላቸው በኋላ ከእርሳቸው ዘንድ በክብር ዐረገ፡፡ ከዚህም በኋላ ጳውሎስ መጥቶ ዮሃንስን ተገናኘው የዚህ አገር ሰዎች ያደረጉብህ ምንድነው እርሱም ስለ እኔ አታድንቅ የሐዋርያትንም አለቃ በእኔ ላይ ባደረጉት አምሳል አድርገውበታልና አለው፡፡ ጳውሎስም አጽናናቸው እንዲህም አላቸው እኔ በጌታችን ፈቃድ ወደ ከተማ ውስጥ ገብቼ እናንተንም አስገባችኋለሁ፡፡

ከዚህም በኋላ ጳውሎስ ሔዶ ምክንያትን ፈጠረ ጣዖታቸውንም እንደሚያመልክ መስሎ ሐዋርያትን እንዲያቀርቡለትና ስለ ሥራቸውም እንዲጠይቃቸው የከተማውን መኳንንት አነጋገራቸው፡፡መኳንንቱም ወደ ጳውሎስ እንዲያቀርቧቸው አዘዙ፤ በቀረቡም ጊዜ ጳውሎስ ስለ ሥራቸው ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም ድንቆችንና ተአምራቶችን ለሚያደርግ ለክርስቶስ ደቀ መዝሙሮቹ እንደሆኑ ነገሩት፡፡ ዳግመኛም እናንተ እንደርሱ ማድረግ ትችላላችሁን አላቸው፡፡ እነርሱም አዎ በእርሱ ስም ሁሉን ሥራ መሥራት እንችላለን አሉት፡፡

ከዚህም በኋላ ከእናቱ ማሕፀን ዕውር ሆኖ የተወለደውን ዐይኑን አበሩ፡፡ የንጉሡንም ልጅ ከሞተ በሦስት ወሩ ሥጋውም ከተበላሸ በኃላ ከመቃብር አስነሡት፡፡ ንጉሡና የከተማ ሰዎች ሁሉ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡ ጴጥሮስም ምድሩን ረግጦ ውኃን አፈለቀ፤ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው በቀናች ሃማኖትም እንዲጸኑ አደረጓቸው፡፡

ከዚህም በኋላ በሎዶቅያ ያሉ ምእመናን የቂሳሮስ ባሕር ከወሰኑ አልፎ ብዙ ሰዎችን ከአትክልት ቦታዎቻቸውና ከከብቶቻቸው ጋራ እንዳሰጠማቸው ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ላኩ፤ ጴጥሮስም ተወዳጅ ዮሐንስን ወደ እነርሱ ላከ፡፡ዮሐንስም ወደ እነርሱ ሲጓዝ ዳና በግ አገኘ፤ በጉንም እንዲህ ብሎ ላከው፤ ወደ ቂሳሮስም ወንዝ ሒድ የክርስቶስ ደቀ መዝሙሩ ወደ አንተ ልኮናል ወደ ቀድሞው ወሰንህ ትገባ ዘንድ አንተ በእግዚአብሔር ቃል የታሰርክ ነህ ብሎሃል በለው፡፡ ያን ጊዜ በጉ እንዳዘዘው አደረገ፤ ወንዙም ሸሽቶ ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡ ቁጥር የሌላቸው ብዙዎች የከተማ ሰዎችም ይህን አይተው በጌታ አመኑ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ አልፎ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ በዚህም ሥፍራ መሠሪው ሲሞን ተቃወመው፤ እርሱንም ከአየር ላይ አውርዶ ጥሎ አጠፋው፤ ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ብዙዎች ሕዝቦች አመኑ፡፡ የከተማው ገዥ የአክሪጶስ ቁባቶችም የጴጥሮስን ትምህርት ተቀበሉ፡፡ ሌሎችም የከበሩ ብዙዎች ሴቶች ትምህርቱን በመቀበል ከባሎቻቸው ርቀው ንጽሕናቸውን ጠበቁ፡፡

ስለዚህም ነገር ቅዱስ ጴጥሮስን ሊገድሉት የሮሜ መኳንንት ተማከሩ፡፡ የአልታብዮስ ሚስትም እንዳይገድሉት ከሮሜ ከተማ ወጥቶ እንዲሔድ ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ላከች፤ ምእመናን ወንድሞችም ውጣ አሉት፤ እርሱም ቃላቸውን ተቀበለ፡፡ ትጥቁንም ለውጦ ከከተማው ወጣ፡፡ በሚወጣበትም ጊዜ መስቀል ተሸክሞ ወደ ከተማ ሲገባ ጌታችንን አገኘውና አቤቱ ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ አለው፡፡ ጌታም ልሰቀል ወደ ሮሜ ከተማ እሔዳለሁ ብሎ መለሰለት፤ ቅዱስ ጴጥሮስም አቤቱ ዳግመኛ ትሰቀላለህን አለው፡፡

ያን ጊዜም ጎልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ እጅህ ታጥቀህ ወደ ወደድከው ትሔዳለህ በሸመገልክ ጊዜ ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል ያለውን የጌታችንን ቃል አሰበ አስተዋለውም፡፡ያን ጊዜም ወደ ከተማው ተመልሶ ክብር ይግባውና ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የሆነውን ለወንድሞች ነገራቸው እነርሱም እጅግ አዘኑ፡፡

ንጉስ ኔሮን ቅዱስ ጴጥሮስን እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ሊሰቅሉትም በያዙት ጊዜ ወታደሮችን እንዲህ ብሎ ለመናቸው፡፤ የክብር ንጉስ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ላይ ሆኖ ስለተሰቀለ እኔ ቁልቁል ልሰቀል ይገባኛል፡፡ ወዲያውም እንደነገራቸው ሰቀሉት፡፡ ተሰቅሎ ሳለም ለምእመናን የሕይወትን ቃል አስተማራቸው በቀናች ሃማኖትም እንዲጸኑ አዘዛቸው ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡ ሰላም ለጳውሎስ ሃይማኖተ ክርስቶስ ዘአግሀደ፡፡ እስከ አቁሰልዎ በሰይፍ ወመተርዎ ክሣደ፡ ከመ ያግብእ ሕዝበ ሕየንተ ቀዳሚ ሰደደ፡፡ በላዕለ አብዳን ተመሰለ አብደ፡፡ ወለአይሁድኒ ኮኖሙ አይሁድ፡፡

በዚህችም ቀን ዳግመኛ ልሳነ ዕረፍት የክርስቶስ አንደበት የእውቀት አዘቅት የቤተ ክርስቲያን መብራት የቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ የሰማዕትነቱ መታሰቢያ ነው፡፡ እንደ ስሙም ትርጓሜ መሪ አመስጋኝ ወደብ ጸጥታ ነው፡፡ይህም ጳውሎስ አስቀድሞ በክርስቶስ ያመኑትን የሚያሳድድ ነበረ፡፡ እርሱም ከብንያም ወገን የፈሪሳዊ ልጅ ነው፡፡ ወላጆቹም ሳውል ብለው ስም አወጡለት፤ ትርጓሜውም ስጦታ ማለት ነው፡፡ ቁመቱ ቀጥ ያለ፤ መልኩ ያማረ፤ ፊቱ ብሩህ፤ ቅላቱ እንደ ሮማን ቅርፍት ደበብ ያለ፤ ዐይኑም የተኳለ የሚመስል አፍንጫው ቀጥ ያለ ሸንጎበታም፤ ጉንጩ እንደ ጽጌረዳ ነበረ፡፡

እርሱም ሕገ ኦሪትን አዋቂ ነበረ፡፡ ለሕጉም ቀናተኛ ሆኖ ምእመናን አሳዳጅ ነበረ፡፡ ወደ ሊቀ ካህናቱም ሔዶ በመንገድ የሚያገኘው ሰው ቢኖር ወንዶችንና ሴቶችን እንደታሠሩ ወደ ኢየሩሳሌም ይመልሳቸው ዘንድ ለደማስቆ ከተማና ለምኩራቦች የፈቃድ ደብዳቤ ለመነ፡፡

ሲሔድም ወደ ደማስቆ ከተማ አቅራቢያ በደረሰ ጊዜ ድንገት ከሰማይ መብረቅ ድንገት ብልጭ አለበት፤ በምድር ላይም ወደቀ፤ ወዲያውም ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ የሚለውን ቃል ሰማ፡፡ ሳውልም አቤቱ አንተ ማነህ አለው፤ አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፤ በሾለው ብረት ላይ ብትረግጥ አንተን ይጎዳሃል አለው፡፡

እየተንቀጠቀጠም አደነቀ፤ አቤቱ ምን እንዳደርግ ትሻለህ አለው፡፡ ጌታም ተነሥና ወደ ከተማ ግባ ልታደርግ የሚገባህን ከዚያ ይነግሩሃል አለው፡፡ ከእርሱ ጋር ቆመው የነበሩ ሰዎችም ንግገሩን ይሰሙ ነበር፤ ነገር ግን የሚያዩት አልነበረም፡፡ ሳውልም ከምድር ተነሣ ዓይኖቹም ተገልጠው ሳሉ አያይም ነበር፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ አስገቡት፡፡ በዚያም ሳያይ ሳይበላና ሳይጠጣ ሦስት ቀን ሰነበተ፡፡

በዚያም በደማስቆ ከደቀ መዛሙርት ወገን ሐናንያ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ ጌታም በራእይ ተገለጠለትና ሐናንያ ብሎ ጠራው፡፡ እርሱም ጌታዬ እነሆኝ አለ፡፡ ተነሥና ቀጥተኛ ወደምትባለው መንገድ ሒድ በይሁዳ ቤትም ጠርሴስ ከሚባል አገር የመጣ ሳውል የሚባል ሰው ፈልግ፤ እርሱ አሁን ይጸልያልና አለው፡፡

ሐናንያ ግን መልሶ እንዲህ አለ፤ አቤቱ ስለዚህ ሰው በኢየሩሳሌም በቅዱሳኖችህ ላይ የሚያደርገውን ክፉ ነገር ሁሉ ከብዙ ሰዎች ሰምቻለሁ፤ ወደዚህም ከካህናቱ አለቃ አስፈቅዶ የመጣ ስምህን የሚጠሩትን ሁሉ ሊያስር ነው፡፡ ጌታችንም ተነሥና ሒድ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና እኔም ስለ ስሜ መከራ ይቀበል ዘንድ እንዳለው አሳየዋለሁ፡፡

ያን ጊዜም ሐናንያ ሔደ፤ ወደ ቤትም ገባ፡፡ ወንድሜ ሳውል በመንገድ ስትመጣ የታየህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታ ዘንድ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይሞላብህ ዘንድ ወዳነተ ልኮኛል አለው፡፡ ያን ጊዜም የሸረሪት ድር የመሰለ ከዐይኖቹ ላይ ተገፎ ወደቀ፡፡ዐይኖቹም ተገለጡ፡፡ ወዲያውም አየ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ እህልም በልቶ በረታ፡፡ ከደቀ መዛሙርትም ጋር በደማስቆ ለጥቂት ቀን ሰነበተ፡፡ በዚያው ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅ ነው ብሎ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰበከ፤ አስተማረም፡፡

የሰሙትም ሁሉ አደነቁ እንዲህም አሉ፤ በኢየሩሳሌም ይህን ስም የሚጠሩትን ያሳድድ የነበረ ይህ አልነበረምን ወደዚህስ የመጣው እያሠረ ወደ ሊቀ ካህናቱ ሊወስዳቸው አይደለምን፡፡ አጽናኝ መንፈስ ቅዱሰም አደረበት ዕውነተኛውንም ሃይማኖት ግልጽ አድርጎ አስተማረ፡፡

ለኦሪት ሕግ የሚቀና እንደነበረ እንዲሁ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠራት ሕገ ወንጌል ዕጽፍ ድርብ ቅንዓትን የሚቀና ሆነ፡፡ ከዚህም በኋላ በአገሮች ሁሉ እየዞረ ሰበከ፤ በጌታችንም ስም ሰበከ፡፡ ድንቆችንና ተአምራትንም አደረገ፡፡ ቁጥር የሌላቸው አሕዛብንም አሳመናቸው ነገር ግን ብዙ ጊዜ በመገረፍ በመደብደብና በመታሠር ብዙ መከራ ደረሰበት፤ መከራውንም ሁሉ ታግሶ በሁሉ ቦታ ዞሮ አስተማረ፡፡

በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንደተጻፈ የእግዚአብሔርን ሥራ ሲሠሩ ሲጾሙና ሲጸልዩ መንፈስ ቅዱስ እኔ እነርሱን ለመረጥሁለት ሥራ ሳውልንና በርናባስን ለዩልኝ አላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ጾመውና ጸልየው እጃቸውንም በራሳቸው ላይ ጭነው ሾሙአቸው፤ ከመንፈስ ቅዱስም ተሹመው ወደ ሴሌውቅያ ወረዱ፡፡

በደሴቱም ሁሉ ሲዘዋወሩ ጳፉ ወደምትባል አገር ደረሱ፡፡ በዚያም ሐሰተኛ ነቢይ የሆነ ስሙ በርያሱስ የሚባል አንድ ሥራየኛ አይሁዳዊ ሰው አገኙ፤ እርሱም ሰርግዮስ ጳውሎስ ከሚባል ብልህ ሰው ከሆነ አገረ ገዥ ዘንድ የነበረ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሊሰማ ወዶ በርናባስንና ሳውልን ጠራቸው፡፡ የስሙ ትርጓሜ እንዲህ ነበርና ኤልማስ የሚሉት ያ ሥራየኛ ሰው ይከራከራቸው ነበረ፤ ገዥውንም ማመን ሊከለክለው ወዶ ነበረ፡፡

ጳውሎስ በተባለው ሳውል ላይም መንፈስ ቅዱስ መላበት፡፡ አተኩሮም ተመለከተው፤ ኃጢአትንና ክፋትን ሁሉ የተመላህ የሰይጣን ልጅ የጽድቅ ሁሉ ጠላት ሆይ የቀናውን የእግዚአብሔርን መንገድ እያጣመምህ ተው ብትባል እምቢ አልህ እነሆ አሁን የእግዚአብሔር እጅ በአንተ ላይ ተቃጥታለች፤ ትታወራለህ እስከ ዕድሜ ልክህም ፀሐይን አታይም አለው፡፡ ወዲያውኑም ታወረ ጨለማም ዋጠው የሚመራውንም ፈለገ፤ አገረ ገዢውም የሆነውን አይቶ ደነገጠ በጌታችንም አመነ፡፡

ከዚህ በኋላ ሒደው ወደ ሊቃኦንያ ከዚያም ወደ ልስጥራንና ደርቤን ከተማ ወደ አውራጃውም ሁሉ ገብተው አስተማሩ፡፡ በልስጥራን ከተማም ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ እግሩ ልምሾ የሆነ አንድ ሰው ነበረ ተቀምጦ ይኖር ነበር እንጂ ልምሾ ከሆነ ጀምሮ ቆሞ አልሔደም፡፡ ጳውሎስንም ሲያስተምር ተመልከቶ ሃይማኖት እንዳለው እንደሚድንም ተረዳ፡፡ ድምጹንም ከፍ አድርጎ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥና ቀጥ ብለህ ቁም እልሃለሁ አለው፤ ወዲያውኑ ተነሥቶ ሔደ፡፡

አሕዛብም ጳውሎስ ያደረገውን አይተው በጌታችን አመኑ፡፡ እርሱም በዚያ ሳለ አይሁድ ከአንጾኪያና ከኢቆንያ መጥተው ልባቸውን እንዲያስጨክኑባቸው አሕዛብንም አባበሉአቸው፡፡ ጳውሎስንም በደንጊያ ደበደቡት፤ ጎትተው ወደ ውጭ አወጡት፡፡በማግስቱም ከበርናባስ ጋራ ደርቤን ከተማ ሔዱ፡፡ በዚያችም ከተማ አስተማሩ ብዙ አሕዛብንም ሃይማኖት አስገቡ ለቤተ ክርስቲያንም ቀሳውስትን ሾሙላቸው፤ ከዚያም ወደ መቄዶንያ አልፈው ሔዱ ጋኔን ሟርት የሚያሥራትን አንዲት ልጅ አገኙ ከምታገኘው ዋጋ ለጌቶቿ ብዙ ትርፍን ታስገባ ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው የሕይወትንም መንገድ ያስተምሯችኋል ብላ እየጮኸች ከጳውሎስ ኋላ ተከተለች፤ ብዙ ቀንም እንዲሁ ታደርግ ነበር፡፡ ጳውሎስንም አሳዘነችው መለስ ብሎም መንፈሰ ርኩስን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንድትወጣ አዝዤሃለሁ አለው ወዲያውኑም ተዋት፡፡

ከዚህ በኋላም ሐለብ ከሚባል አገር ደረሰ፤ የጢሞቴዎስንም እናት ስሟ በድሮናን ከሞት አስነሣት፡፡ በዚያም ያዙት ለዚያች አገር ጣኦትም ሊሠዉት ወድደው በሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት፡፡ ስለ እነርሱም እየማለደ እጆቹን በመስቀል ምልክት አምሳል ዘረጋ፡፡ አሕዛብም በአዩት ጊዜ ስለዚህ ድንቅ ሥራ አደነቁ፤ ከእሳት መካከልም እንዲወጣ ማለዱት፤ ምንም ምን ሳይነካው ወጣ ሰገዱለትም ክብር ይግባውና በጌታችንም አመኑ የአገሩ ሹም አርስጦስም አመነ፡፡

ሰባቱ የጣዖት ካህናት ግን ሸሽተው ተሠወሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በጭላት አምሳል የተቀረጸውን ምስል ጠራው ምስሉም በአንባሳ አምሳል መጥቶ በምኩራቡ መካከል በጳውሎስ ፊት ቆመ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የሚያመልኩህ ካህናቶችህ ወዴት አሉ አለው፤ አንበሳውም ያሉበትን አስክነግርህ ድረስ ጌታዬ ጥቂት ታገሠኝ፤ አለው፡፡ ካህናቱም ወደተሸሸጉበት ሔዶ አንዱን አንገቱን በአፉ ይዞ እየጎተተ አምጥቶ እንደ በድን በአደባባዩ መካከል ጣለው፡፡ ሰባቱንም እንዲሁ እያንዳንዱን እየጎተተ አመጣቸው፡፡

ሕዝቡም ሊገድሏቸው ወደዱ፡፡ ጳውሎስም ዛሬ በዚህች ከተማ ማዳን እንጂ መግደል አይገባም አለ፤ ከዚህም በኋላ ሁሉንም አጠመቃቸው፤ ሃይማኖትንም አስተማራቸው፡፡ ያንንም አንበሳ የሆነ የጭላት ምስል አንበሳ ሆይ አትፍራ ስለ አገለገልከኝ እሰከምሻህ ድረስ ኑሮህ በበረሀ ይሁን አለው ያን ጊዜም ወደ በረሀ ሔደ፡፡

ጳውሎስም ከዚያ ተነስቶ አካ ወደሚባል ከተማ ሔደ፡፡ ስክንትስ ከሚባል ደቀ መዝሙርም ጋር ተገናኘ፤ አይሁድም ዜናውን ሰምተው ከአሕዛብ ጋራ ተሰበሰቡ ይዘውም ጭንቅ የሆነ ስቃይን አሰቃዩት፤ ዳግመኛም ሁለት በሮችን አመጡ ከስክንጥስ ጋራም አሥረው በከተማው ጥጋጥግ በስለታም ድንጋይ ላይ አስጎተቷቸው ደማቸውም እንደ ውኃ ፈሰሰ፤ አጥንታቸውም እሰከሚታይ ድረስ ሥጋቸውም ተቆራረጠ፡፡ ወደ ጌታም ጸለዩ፤ ያን ጊዜም በሮቹ ከሚነዳቸው ጋራ ደንጊያ ሆኑ፡፡

ሕዝቡም በአዩ ጊዜ ለመኮንኑ ነገሩት እርሱም ተቆጣ ወደ እርሱም እንዲያቀርቧቸውና በደንጊያ እንዲወግሯቸው አዘዘ፤ በቅዱስ ጻውሎስም ላይ እጅግ ተቆጥቶ አንተ የሥራይ ሰው እነሆ አሠቃይሃለሁ አለው፡፡ በበሬ ቅርጽ የተሠሩ ሁለት ቀፎዎችንም ያመጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ዝፍት ሙጫና ድኝ አምጥተው በውጭ ቀላለቅለው ሁለቱን የናስ ቀፎዎች በውስጥም በውጭም ቀቧቸው፡፡ ሐዋርያትንም በውስጥ ጨምረው በእሳት ምድጃ ውስጥ አስገቧቸው፤ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊትም እሳት አነደዱባቸው፡፡

መድኃኒታን ኢየሱስ ክርስቶስም ከመላእክቶቹ ጋራ መጣ እሳቱንም ከዚያ ፈልሶ ወደ ከተማ ውሰጥ ገብቶ የከተማውን ሰዎች ሁሉ እንዲከባቸው አደረገው፤ በተጨነቁም ጊዜ ጮኹ፤ አለቀሱም፡፡ መዳንን ከፈለጋችሁ ፈጥናችሁ በአደባባዩ በአንድነት ተሰብሰቡ የሚል ቃል ከሰማይ ጠራቸው፡፡ ጳውሎስም ወደ በረሀ አሰናብቶት የነበረው አንበሳ መጣ፤ ጳውሎስ በስሙ በሚያስተምርበት ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ እያለ ጮኸ፡ ከዚህም በኋላ ወደ እሳቱ ምድጃ ተመልሶ ጳውሎስንና ስክንጥስን ከእሳቱ ውስጥ ውጡ አላቸው፤ ያን ጊዜም የራሳቸው ጠጉር እንኳ ሳይቀነብር ወጡ፤ በላያቸውም ላይ የቃጠሎ ሽታ የለም፡፡

ይህንን ድንቅ ሥራ አይተው በጌታችን በናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን እያሉ ጮኹ፤ ከዚህም በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው ስክንጥስንም ቅስና ሾመላቸው፡፡ከዚህ በኋላም ከሐዋርያ ፊልጶስ ጋራ ወደ ሁለት አገሮች በአንድነት ሔዱ፤ በዚያም በጌታችን ስም ሰበኩ የአገሩ አለቆችም ያዙአቸው እጆቻቸውንና እግሮቻቸውንም አሠሩአቸው በአንገቶቻቸውም የብረት ሰንሰለቶችንም አስገቡ ራሳቸውንም የሚሸፍን የብረት ቆብን ሠሩላቸው ዳግመኛም በእጅና በመሐል እጅ ጣቶችም ምሳሌ ሠርተው በእጆቻቸውና በክንዶቻቸው እያንዳንዱን የብረት እጅ ጨመሩ፡፡ ከብረቶችም ጋር ቸነከሩአቸው፡፡

ሁለተኛም እስከ አንገት የሚደርስ በትከሻ አምሳል ሠሩ፤ በፊትና በኋላም ቸነከሩአቸው፡፡ ደግሞም መላ አካላቸው ምንም እንዳይታይ የሚሽፍን የብረት ሠሌዳ ሠሩ፡፡ ከወገቦቻቸውም ጋራ ቸነከሩት፤ ችንካሮችም ተረከዛቸውን ነድለው ወደ ጭኖቻቸው እስከሚደርሱና እሰከ አቆሰላቸው ድረስ የብረት ጫማ ሠርተው እግሮቻቸውን ቸነከሩ፡፡

ደግሞ በመሸፈኛ አምሳል የብረት ሰናፊል ሠሩ፤ ቀማሚዎችም መጡ አንድ መክሊት የሚመዝን እርሳስንም አመጡ ታላቅ የብረት ጋንንም ሰባት ልጥር የሰሊጥ ቅባትን አመጡ፡፡ ስቡንና አደሮ ማሩን የእሳቱንም ኃይል አብዝቶ የሚነደውን ቅመሙን ከሙጫውና ከድኙ ጋር ቀላቀሉ፤ ከዋርካና ከቁልቋል ከቅንጭብም ደም ሰባት ልጥር አንድ የወይን አረግንና ቅባት ያላቸውን ዕንጨቶች ሁሉ አመጡ፡፡ በጋን ውስጥ ያበሰሉትንና ያሟሙትንም ልዩ ልዩ ቅመማ ቅመም አምጥተው ከሥጋቸው ጋራ እሰከሚጣበቅ በቅዱሳን ሐዋርያት ሥጋ ላይ ባሉት ሠሌዳዎች ውስጥ ጨመሩት፡፡ ከእግራቸው አስከ ራሳቸውም ከፍ ከፍ እስከሚል ድረስ በእሳት ያቃጠሉትን ያንን እርሳስ ጨመሩ፡፡ ርዝመቱ ዐስራ አምስት ክንድ በሆነ ወፍራም የጥድ ምሰሶ ላይም አቆሟቸውና ከበታቻቸው ፍሬ በሌለው በወይን ሐረግና በተልባ እሳቱን አቀጣጥለው አነደዱ፡፡ የእሳቱ ነበልባልም ከሥጋቸው በላይ ከፍ ከፍ አለ ሐዋርያ ግን ወደ እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፡፡

ከመኳንንቱም በአንዱ ልብ ርኅራኄን አሳደረና እንዲፈቷቸው አዝዞ ፈቷቸው፡፡ በፈቷቸውና ሠሌዳውን ከሥጋቸው ላይ ባስወገዱ ጊዜ ቆዳቸው ተገፈፈና ከብረቱ ሠሌዳዎች ጋራ ወጣ፡፡ ብዙ ደምም ከሥጋቸው ጋር ፈሰሰ፡፡ ሰይጣንም በከተማው ሰዎች ልብ አደረና ሐዋርያትን ወደ እሳት ውስጥ መለሱአቸው፤ ያን ጊዜ ጌታችን ወርዶ የእሳቱን ነበልባል አጠፋው፡፡ ዝናምን የተመላች ብርህት ደመናም መጥታ ቅዱሳን ሐዋርያትን ከበበቻቸው፤ በዚያችም አገር አንድ ጊዜ በደንጊያ በመውገር አንድ ጊዜም በፍላጻ በመንደፍ ብዙ ተሠቃዩ፡፡ ከዚህም በኋላ ሙታንን በአነሡ ጊዜ የከተማው ሰዎች ሁሉ አመኑ፤ አጠመቋቸውም፤ ቤተ ክርስቲያንንም ሠሩላቸው፤ ካህናትንም ሾሙላቸው በቀናች ሃይማኖትም እስቲጸኑ አስተማሩአቸው፡፡ ከዚያም ወጥተው ጌታችን ወዳዘዛቸው ወደ ሌላ አገር ሔዱ፡፡

ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጳውሎስ ተገለጠለትና የመረጥኩህ ጳውሎስ ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን፡፡ መታሰቢያህን የሚያደርገውን፤ በስምህ ቤተ ክርስቲያን የሚሠራውንና፤ በውስጧም የሚጸልየውን ስለትንና መባንም የሚሰጠውን በመታሰቢያህም ቀን ለድሆች የሚመጸውተውን ሁሉ ካንተ ጋራ በመንግሥተ ሰማያት አኖራቸዋለሁ አለው፡ በስምህ የታነጹትንም አብያተ ክርስቲያናት መላእክቶቼን እንዲጠብቋቸው አደርጋቸዋለሁ፤ ብዙ ቃል ኪዳንም ሰጠው፡፡ በመለኮታዊ አፉ አፉን ሳመውና ከእርሱ ዘንድ ወደሰማያት በክብር ዐረገ፡፡

ከዚህም በኋላ እልዋሪቆን ወደምትባል ታላቅ ሀገር እስከሚደርስ በብዙ አገሮች ውስጥ ተመላለሰ፡፡ በዚያም የብርሃን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጻለት አረጋጋቸው፤ ረዳቸውም፡፡ በመጋቢት 29 እንደጻፍነው የአገሩን ሰዎች እንዲያጠምቃቸውና እንዲያስተምራቸው አዘዘችው፡፡

ከዚህም በኋላ ወደ ሮሜ ከተማ ገብቶ በውስጧ ሰበከ፤ በስብከቱም ብዙ ሰዎች አምነው የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው፡፡ በመጻሕፍትነት ያታወቁ ዐሥራ አራት መልእክቶችን ጻፈ፤ የመጀመሪያ መልእክቱም ለሮሜ የተጻፈችው ናት፡፡ መልካም ሩጫውንም ከፈጸመ በኋላ ንጉሥ ኔሮን ይዞ ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው፡፡ ራሱንም በሰይፍ እንድቆርጡት ለሰያፊ ሰጠው፤ ከሰያፊውም ጋራ አልፎ ሲሔድ ከንጉሥ ኔሮን ዘመዶች ወገን የሆች አንዲት ብላቴና አገኘቸው፤ እርሷም ክብር ይግባውና በጌታችን ያመነች ነበረች፤ ለእርሱም አለቀሰች፡፡ እርሱ ግን መጎናጸፊያሽን ስጪኝ እኔም ዛሬ እመልስልሻለሁ አላት፡፡ እርሷም መጎናጸፊያዋን ሰጠችውና ራስ ወደሚቆርጡበት ቦታ ሔደ፡፡ ለሰያፊውም ራሱን ባዘነበለ ጊዜ በመጎናጸፊያዋ ፊቱን ሸፈነ፤ ሰያፊውም የቅዱስ ጳውሎስን ራስ ቆርጦ በዚያች ብላቴና መጎናጸፊያ እንደተሸፈነ ጣለው፡፡

ሰያፊውም ጳውሎስን እንደገደለው ለንጉሥ ሊነግረው በተመለሰ ጊዜ ያቺ ብላቴና አገኘቸው፤ ያ ጳውሎስ ወዴት አለ አለችው ራስ በሚቆረጥበት ቦታ ወድቋል ራሱም በመጎናጸፊያሽ ተሸፍኗል አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ ዋሽተሃል እነሆ ጴጥሮስና ጳውሎስ በእኔ ዘንድ አልፈው ሔዱ እነርሱም የመንግሥት ልብሶችን ለብሰዋል፤ በራሳቸውም ላይ በዕንቁ የተጌጡ ዐይንን የሚበዘብዙ አክሊላትን አድርገዋል፡፡ መጎናጸፊያዬንም ሰጡኝ፤ አርሷም እነኋት ተመልከታት ብላ ለዚያ ሰያፊ አሳየችው ከእርሱ ጋራ ለነበሩትም አሳየቻቸው፡፡ አይተውም አደነቁ፤ ስለዚህም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡የዚህም ሐዋርያ ጳውሎስ ተአምራቶቹ ቁጥር የሌላቸው እጅግ የበዙ ናቸው፡፡
ለእግዚአብሔር ምሥጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት፤ ከሁሉም ሊቃነ ጳጳሳት፤ እና የቅድስት የሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡
ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ
http://eotcmk.org/site/-mainmenu-24/--mainmenu-26/1514--6