Monday, May 20, 2013

የቅዱስ ያሬድን 1500ኛ የልደት በዓል አስመልክቶ የተዘጋጀ ዐውደ ጥናት ተከፈተ


ዲ/ን መርሻ አለኸኝ(ዶ/ር)
የቅዱስ ያሬድን 1500ኛ የልደት በዓልን ምክንያት በማድረግ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የተዘጋጀ ዐውደ ጥናት በግዮን ሆቴል ሳባ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተከፈተ፡፡ በዐውደ ጥናቱ ላይ  ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያዎች ሓላፊዎች፣ በዋና ዋና አብነት ት/ቤቶች የሚያስተምሩ መምህራንና የመንግሥትና ልዩ ልዩ ተቋማት ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው ሊቃውንት ተገኝተዋል፡፡

ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ማኅበሩ ቅዱሳት መካናት ራሳቸውን ችለው የሚተዳደሩባቸውን ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽና በመተግበር ለአብነት መምህራንና ተማሪዎች ድጋፍ በማድረግ ከፍተኛ ሥራ አየሠራ እንደኾነ ከገለጹ በኋላ፤ ሊቁ ለሀገራችን ከሰጠው አበርክቶ አንጻር ማኅበሩ ከፍተኛ ቦታ የሚሰጠውን የቅዱስ ያሬድን የ1500ኛ ዓመት የልደት በዓል በሰፊ ዝግጅት ለማክበር እንደወሰነ ገልጸዋል፡፡

Friday, May 10, 2013

የቀኝ ዐይን - ድንግል ማርያም



በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ
አፍጣኒተ ረድኤት ማርያም በጊዜ  ምንዳቤ ወአጸባ ለዐይን እምቀራንባ፤ አንቲ ውእቱ ረዳኢተ ያዕቆብ በቤተ ላባ፤ በኩሉ ኅሊናሃ ወበኩሉ አልባባ፤ዘኢታፈቅረኪ ነፍስ ትሠሮ እምሕዝባ፡፡

lidetaleMariam

የነገረ ማርያም ሊቅ(Marian Doctor)እየተባለ የሚጠራው ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ እመቤታችንን በብዙ ምሳሌ እየመሰለ፣ እየተረጎመና እያመሰጠረ ብዙ ጊዜ አመስግኗታል፡፡ ምንም እንኳን እኛ የምናውቀው የምስጋና ድርሰቱ ለጸሎት የምንጠቀምበት ውዳሴ ማርያም ቢሆንም ከትርጓሜና ከስብከቶቹ ውጪ ከሦስት ሚሊዮን በላይ ስንኝ ያላቸው የምስጋና ድርሰቶችን(Hymns) መድረሱን ታሪክ ጸሐፊው ሶዝመን መዝግቦልናል፡፡ ከነዚህ የምስጋና ድርሰቶቹ መካከልም ‹‹በእንተ ልደት››(On Nativity) እና ‹‹በእንተ ቤተ ክርስቲያን››(On the Church)በተባሉ ትልልቅ ድርሰቶቹም እመቤታችንን ደጋግሞ ያመሰግናታል፡፡

Sunday, April 28, 2013

ሰሙነ ሕማማት


መምህር ኃይለ ማርያም ላቀው

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከትንሣኤ በፊት ያለውን አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት /የሕማማት ሳምንት/ በማለት ትዘክረዋለች፡፡ ሕማማት የሚለው ቃል “ሐመ፤ ታመመ” ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን የጌታችንና የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕማምና ሞቱ የሚዘከርበት ሳምንት ነው፡፡ በሌላም በኩል ይህ ሳምንት ከአዳም እስከ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ የነበሩ ነፍሳት በሲኦል የቆዩበት የአምስት ሺህ አምስት መቶ የመከራ፣ የፍዳና የኩነኔ ዘመን መታሰቢያ ስለሆነ የሕማማት ሳምንት የሚለውን ስያሜ አግኝቷል፡፡ እንደዚሁም ይህ ሳምንት “ቅዱስ ሳምንት” ይባላል” ከሌሎች ሳምንቶች ሁሉ የተለየ የከበረ ነውና፡፡ ምክንያቱም በዚህ ሳምንት በእያንዳንዱ ዕለት ስለ ፍጹም ፍቅር የተከፈለ የመሥዋዕትነት ሥራ ስለ ተሠራበት፣ የሰው ልጆች ደኅንነት ስለ ተፈጸመበት፣ መድኀኔዓለም ስለ እኛ ቤዛ ሆኖ ለመስቀል ሞት ታዛዥ ሆኖ ነፍሱን ስለ ካሠልን “ቅዱስ ሳምንት” ተብሏል፡፡ በተጨማሪም “የመጨረሻ ሳምንት” ተብሎ ይጠራል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በሙዓለ ሥጋዌው ለፈጸማቸው የቤዛነትና የአርአያነት ተግባራት ፍጻሜ በመሆኑ ነው፡፡
በዚህ ልዩ በሆነ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠልስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን ኢየስስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ምዕራፍ ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ያዘክራሉ፤ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ያዘጋጀውን መዝሙር ይዘምራሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡

Sunday, April 14, 2013

ገብርኄር


በዲ/ን አባተ አስፋ
ዛሬ ታላቁን የጌታችንን ጾም ከጀመርን ስድስተኛ ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ሳምንት ቅድስት ቤተክርስቲያን «ገብርኄር» የሚል ስያሜ ሰጥታዋለች፡፡ ገብርኄር በጎ አገልጋይ ማለት ሲሆን የስያሜውን መነሻ የምናገኘው በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሚነበበው የወንጌል ክፍል ማቴ.25-14-30 ነው፡፡
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ መስሎ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል አንዱ የሆነው ይህ የዛሬው ወንጌል አስተማሪ የሆኑ መሠረታዊ ጉዳዮችን በውስጡ ይዟል፡፡ በተለይ ምንም እንኳን የቤተክርስቲያን ሓላፊነት የእገሌና የእገሊት ተበሎ ባይወሰንም ቤተ ክርስቲያን ባላት የአገልግሎት መዋቅር መሠረት የሓላፊነትን ቦታ ይዘው ለሚያገለግሉ ሰዎች አትኩሮት ሊሰጡባቸው የሚገባቸውን ነጥቦች ይጠቁማል፡፡ ይህን ለማየት ያመቸን ዘንድ ከታሪኩ የመጀመያ ክፍል በመነሣት ዋና ዋና የሆኑ ዐሳቦችን በአትኩሮት መመርመር ጠቃሚ ነው፡፡

Sunday, April 7, 2013

ደብረ ዘይት


በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ
የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድ ነው?/ማቴ. 24፣3/

በዓቢይ ጾም ውስጥ ካሉት ሳምንታት ደብረ ዘይት 5ኛው ሳምንት ላይ ይውላል፡፡ ደብረ ዘይት ትርጉሙ የወይራ ዛፍ ተራራ ማለት ሲሆን፣ ይህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኢየሩሳሌም በሚገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ቅዱሳን ሐዋርያት” የዓለሙ ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድነው?”/ማቴ. 24፣3/ ብለው ጠይቀውት እርሱም የማይቀረውን የዓለም ፍጻሜና አስቀድመው የሚፈጸሙ ምልክቶችን አስረድቷቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ በደብረ ዘይት ሳምንት ታስበዋለች፤ ለምእመናኑም ከዘመኑ ሁኔታ አንጻር በመጻሕፍት የተጠቀሱትን የትንቢት ምልክቶቹን ከተግባራዊ የዓለም ክንዋኔዎች አንጻር በማገናዘብ ታስተምራለች፡፡ በመሆኑም በቤተ ክርስቲያናችን በደብረ ዘይት ሳምንት ምጽአትን አስመልክቶ የሚነገሩ ምስጢራት እጅግ ሰፊ ናቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ጽሑፍ በመጠኑ የምናየው ከቅዱሳት መጻሕፍት አንጻር በዓለም እየተከሰቱ ካሉ ወቅታዊ ምልክቶች ጋር በማገናዘብ ይሆናል፡፡

Tuesday, March 12, 2013

አርባ መአልትና አርባ ሌሊት ጾመ ማቴ.4፥2


በመ/ር ምሥጢረሥላሴ ማናየ
ይህ ከላይ ያነሣነው ርዕስ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንና አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አርባ መአልትና አርባ ሌሊት መጾሙን ያስተምረናል፡፡
በዚህ ኀይለ ቃል ሁለት ታላላቅ ቁም ነገሮችን ቃላትን እንመለከታለን

  1. አርባ መአልትና አርባ ሌሊት
  2. ጾም የሚሉት ናቸው፡፡

በቅድሚያ አርባ መአልትና አርባ ሌሊት የሚለውን ከእነ ምስጢሩ እንመለከተዋለን፡፡ ቀጥለን ደግሞ ጌታችንስ ለምን አርባ መአልትና አርባ ሌሊት ጾመ? የሚለውን እንመለከታለን እግዚአብሔር አይነልቡናችንን ይክፈትልን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን የፈጠረውን የሰው ልጆችን አባት አዳምን፣ በልጅነት አክብሮ ገነት ያስገባው በፈጠረው በአርባ ቀኑ ነው፡፡ “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ እግዚአብሔር ዘገብሮ ለአዳም” አዳምን የፈጠረ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው እያሉ እያመሰገኑ መላእክት ወደገነት አስገብተውታል /ቀሌ.4፥/

Saturday, March 9, 2013

የዐቢይ ጾም ስብከት


በአያሌው ዘኢየሱስ

ሐዋርያዊትና ኦርቶዶክሳዊት በሆነችው በቅድስቲቱ ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ጾም እንደ እንግዳ ደራሽ፤እንደ ወንዝም ፈሳሽ በድንገት የተጀመረ ሥርዓተ አይደለም፡፡ በተለይም በአዲስ ኪዳን ዘመን ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይሆን መድኀኒታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ የመጀመሪያ አድርጎ የሠራው ሕግ ነው፡፡ ጌታ በመዋዕለ ስብከቱ በአንድ ወቅት ከመጥምቁ ዮሐንስና ደቀ መዛሙርት ጾምን አስመልክቶ የቀረበለት ጥያቄና የሰጠው መልስ አለ፡፡ ያቀረቡለት ጥያቄ፡- «. . .  እኛና ፈሪሳውያን ብዙ ጊዜ የምንጦመው፤ ደቀ መዛሙርትህ ግን የማይጦሙት ለምንድር ነው?» (ማቴ 914)  የሚል ነበር፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጣቸው መልስ እንዲህ የሚል ነበር፡- «. . . ሚዜዎች ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሊያዝኑ ይችላሉን; ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወሰድበት ወራት ይመጣል፤በዚያን ጊዜም ይጦማሉ፡፡» ማቴ 915፡፡ ጌታ በዚህ መልሱ ውስጥ ራሱን  በሙሽራ ደቀ መዛሙርቱንም በሚዜዎች በመመሰል እርሱ በመንፈስ ሳይሆን በሥጋ ከእነርሱ በዕርገቱ ተለይቶ ከመሔዱ በፊት ሊያዝኑ፣ ሊተክዙና ከመባልዕት ሊከለከሉ እንደማይችሉ ነገር ግን በዕርገቱ ሲለያቸው መጾም እንደሚጀምሩ ተናገረ፤አስተማረ፡፡ በመሆኑም «በዚያን ጊዜም ይጦማሉ፡፡» የሚለው ሐረግ እርሱ በገዳመ ቆሮንቶስ የጣለውን የጾም መሠረት እነርሱ ከዕርገቱ በኋላ አጠናክረው እንደሚቀጥሉበት የሚያጎላ ነው፡፡