Monday, February 25, 2013

ፍርድ ለነነዌ÷ ሥልጣን ለነነዌ




በዲ/ን ዮሴፍ ይኩኖአምላክ

ኮናኔ በርትዕ÷ ፈታሄ በጽድቅ÷ የሆነው መድኀኒዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ጻፍት ፈሪሳውያንን በቋንቋቸው በዕብራያስጥ ቢያስተምራቸው “እንደ ሙሴ፡- ባሕር ከፍለህ÷ ጠላት ገድለህ÷ ደመና ጋርደህ÷ መና አውርደህ፣ እንደ ኢያሱ፡- በረድ አዝንመህ÷ ፀሐይ አቁመህ÷ እንደ ጌዴዎን፡- ፀምር ዘርግተህ ጠል አውርደህ፣ እንደ ኤልያስ ሰማይ ለጉመህ እሳት አዝንመህ ልታሳየን እንወዳለን” የሚል ጥያቄ በቀረበለት ጊዜ የሰጣቸው ምላሽ “ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል÷ ከነቢዩ ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት  አይሰጠውም፡፡ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ÷ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል፡፡ የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈረዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና÷ እነሆም ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ” የሚል ነው፡፡ ጻፍት ፈሪሳውያንን ምልክት ያስፈለጋቸው ዋነኛ ምክንያት በጌታችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ለማመን አልነበረም፤ ይልቅስ እንደ ዘማ ሴት ምልክት በምልክት እየተደራረበ ማየትን በመናፈቅ ነው፡፡

Friday, February 15, 2013

የየካቲት ኪዳነ ምህረት ዓመታዊ ክብረ በዓል

                                      በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! 

በሀገረ ቤልጅየምና በዙሪያዋ ለምትኖሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን በሙሉ፤  

 በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በእናታችን በወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም ስም መንፈሳዊ  ሰላምታችንን እያስቀደምን: እንኳን ለእናታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ ክብረ በዓል በሠላም አደረሳችሁ። የካቲት ኪዳነ ምህረትን በዓል በዕለቱ የካቲት 16 2005. (Feb 23, 2013) ከዋዜማው (የካቲት15, Feb.23) ጀምሮ; ከየአጥቢያ ቤተክርስቲያን ሚመጡ አባቶች ና ምእመናን በሚገኙበት ሌሊት በማኅሌት እና  ጠዋት በቅዳሴ በደመቀ ሁኔታ ይከበራል። ቤተክርስትያኗ ከዋዜማው ምሽት 22፡00 ሰዓት ጀምሮ ክፍት ስለምትሆን በሰዓቱ ተገኝተው ከልዩ ልዩ የአዳር መርሐ ግብሮች ተካፋይ እንዲሆኑና ሌሎችንም እንዲጋብዙ ቅድስትቤተ-ክርስቲያን ጥሪዋን ታስተላልፋለች።  ሕንፃ ቤተ-ክርስትያኑ ከእኩለ ቀን (11፡30) በሗላ ለሌላ አገልግሎት ስለሚፈለግ በሰዓቱ ቀደም ብለው በመገኘት የበረከቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ በትህትና እንጋብዛለን።   ይህ መልዕክት የማይደርሳቸውን ምዕመናንንም በመቀስቀስ የበረከቱ ተሳታፊ እናድርጋቸው።             

 የአምላካችን ረድኤት የቅድስት ኪዳነ ምሕረት አማላጅነት ከሁላችን ጋር ይሁን።

Tuesday, February 5, 2013

“የዲያብሎስን ሥራ ይሽር ዘንድ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ፡፡” 1ኛ ዮሐን.3፥8




ምንጭ :ከማህበረ ቅዱን ድህረ ገፅ የተወሰደ
በዲ/ን ኃይለ ኢየሱስ ቢያ
ይህንን ኀይለ ቃል የተናገረው  ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ነው፡፡ የተናገረበት ምክንያት፡-
የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ የጌታችን መድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መገለጥ /ሰው ሆኖ የማዳን ሥራውን/ መፈጸሙን ለመግለጥ  የተናገረው /የጻፈው ኀይለ ቃል ነው፡፡
  • መገለጥ ማለት ፡- ረቂቁ አምላክ በተአቅቦ ርቀቱን ሣይለቅ ውሱን ሥጋን ውሱኑም ሥጋ በተአቅቦ ውስንነቱን ሳይለቅ ረቂቅ መለኮትን የሆነበት በአጭር ቃል የቃል ግብር ለሥጋ የሥጋ ግብር ለቃል የሆነበት ረቂቅ ምስጢር ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቀዳማዊ ደኃራዊ የሆነው አምላክ ሞት የሚስማማው ሆነ፤ ዘመን የሚቆጠርለት ሥጋ ዘመን የማይቆጠርለት ሆነ፡፡ ሥጋ በማይመረመር ምስጢር የመለኮትን ገንዘብ ገንዘቡ ቢያደርግ “ፊተኛውና መጨረሻው ሕያውም እኔ ነኝ ሞቼም ነበርሁ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ” /ራእ.1፥17/ ማለት የቻለበት ምስጢር ነው፡፡ የረቀቀው ገዝፎ የገዘፈው ረቆ፣ ሰማያዊው ምድራዊ  ምድራዊው ሰማያዊ ሆኖ መታየት ማለት ነው፣  ከዓለም ተሰውሮ የነበረው ምስጢር  ግልጥ ሆኖ መታየት ማለት ነው ይህንንም ምሥጢር ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጢሞቴዎስ  መልእክቱ “እግዚአብሔርን የመምሰል ምስጢር ያለጥርጥር ታላቅ ነው፤ በሥጋ የጠገለጠ፣ በመንፈስ የጸደቀ፣ ለመላእክት የታየ፣ በአሕዛብ የተሰበከ፣ በዓለም የታመነ፣ በክብር ያረገ /1ጢሞ 3፥16/ በማለት፡፡ ከልደት እስከ ዓቢይ ጾም መጀመሪያ  ያለው ጊዜ  ዘመነ አስተርእዮ /የመገለጥ ዘመን/ የመታየት ወቅት ይባላል::

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ በፍጹም ተዋሕዶ ሰው መሆኑን /ዓለምን ለማዳን መወለዱን የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡

የእግዚአብሔር መገለጥም በ3 ዘመናት ከፍሎ ማየት ይቻላል