Wednesday, November 1, 2017

የኤልሳዕ ማሰሮና ማድጋ የአምላክ እናት



 በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ 
 በረከቱ ይደርብንና የነቢዩ ኤልሳዕ በዐለ ዕረፍት ጥቅምት 20 ሲኾን፤ የኤልያስ መንፈስ ዕጥፍ የኾነለት፤ የኢያሪኮን ውሃ በጨው ያጣፈጠ ነው፤ ጨው የጌታ፤ ዐዲስ ማድጋ የእመቤታችን ምሳሌ ነው፤ በፍዳ በመርገም የመረረችውን ዓለም ያጣፈጠ የዓለም መድኀኒት ክርስቶስን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ወልዳ ያስገኘችልን እናታችን ድንግል ማርያምም የኢያሪኮን ውሃ ምረት ያስወገደውን ጨው በያዘችው በኤልሳዕ ዐዲስ ማሰሮ ትመሰላለች (፪ነገ ፪፥፳)፡፡
 ነቢየ እግዚአብሔር ኤልሳዕ መምህሩ ኤልያስን ሸኝቶ ዮርዳኖስን ተሸግሮ ኢያሪኮ ደረሰ፤ ወደዚያው ገብቶ “ሠናይት ንብረታ ለዛቲ ሀገር” አለ፤ የከተማይቱም ሰዎች ኤልሳዕን “እነሆ ጌታችን እንደሚታይ የዚች ከተማ ኑሮ መልካም ነው” ወማየ ብሔሩሰ እኩይ ውእቱ የአገሩ ውሃ ግን ክፉ ነው፤ "አንስትኒ ይመክና" ወላዶች ሴቶች ሲጠጡት ይመክናሉ ደኽነኛው ሰውም ቢጠጣው በሽተኛ ይኾናል አሉት።
ኤልሳዕም “በውስጡ ጨው ጨምራቸው ዐዲስ ማሰሮ አምጡልኝ” አላቸው፤ እነሱም አመጡለት፤ ኤልሳዕም ውሃው ወዳለበት ምንጭ ወጥቶ፤ ጨው ጨምሮ ማሰሮውን ከቀበረ በኋላ “እግዚአብሔር እንዲኽ ይላል ይኽነን ውሃ ፈውሼዋለኊ፤ ከዚኽም በኋላ ሞትና ጭንገፋ አይኾንበትም” አለ፡፡ ከዚያ ቀን ዠምሮ ውሃው ከምረቱ ተለውጦ ጣፍጦ በሽተኛ ቢጠጣው ጤነኛ፤ መካን ብትጠጣው የሚያስወልድ ኹኗል (፪ነገ ፪፥፲፱-፳፪)፡፡
 ለጊዜው እንዲኽ ተደርጓል ለኋላው ግን ምሳሌ ነበር፤ የውሃውን ምረት ያጠፋውን ጨው የያዘችው ዐዲስ ማሰሮ፤ ከዓለም ፍዳ መርገምን ያጠፋ ጌታን የወለደች የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትኾን፤ ጨዉ የጌታ፤ ውሃው የዚኽ ዓለም፤ ምረት የፍዳ የመርገም ምሳሌ ነበር፡፡
❖ ኢትዮጵያዊዉ ሊቅ አባ ጊዮርጊስም ይኽነን ልዩ ምሳሌ ሲተረጒም "ኤልሳዕ ካዕበተ መንፈሱ ለሊቁ ነሥአ …” (ኤልሳዕም በመምህሩ ያደረ መንፈስ ቅዱስን ዕጥፍ ድርብ አድርጎ ተቀበለ፤ በመጠምጠሚያውም ምት የዮርዳኖስን ባሕር ከፈለው፤ የመጥረቢያውን ብረትም በውሃ ላይ አንሳፈፈው፤ ብዙ ተአምርንም ዐደረገ፤ ሙታንን አነሣ፤ በዮርዳኖስ ውሃ ለምጻሙ ንእማንን አነጻው፤ የሚያመክነውንም የውሃ ምረት በጨው አጣፈጠ፤ መካኖች የሚኾኑ የዚያ ሀገር ሰዎች ይወልዱ ዘንድ (፪ነገ ፪፥፲፱-፳፩፤ ፭፥፲፬፤ ፮፥፮-፯)፤ ከኀጢአት ማንጻትን የነፍስንም ምረት ማጣፈጥን ግን አልቻለም፤ ልጅሽ ግን የሥጋ ለምጻሞችን አነጻቸው፤ ዳግመኛም የዓለሙን ምረት በመለኮቱ ጨውነት አጣፈጠ፤ ኹለተኛም ውሃውን አጣፍጦ የወይን ጠጅ ዐደረገው) (ማቴ ፰፥፪-፫፤ ዮሐ ፪፥፰-፱)) ፤ በማለት ለ፭ሺሕ ፭፻ ዘመን ከመድኀኒቷ ተለይታ፤ አልጫ ለኾነችው ዓለም መድኀኒት የኾነ መድኀኔዓለም ክርስቶስን ያስገኘችልን መኾኗን አስተምሯል፡፡
 ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም በመጽሐፉ ላይ ይኽነን ሲያብራራ ‹‹አንቺን በሐዲስቱ ማሰሮ ገለጠሽ፤ ልጅሽም ለምንጩ ዐዲስ ሕይወትን የሰጠ ጨው ነው፤ በሱም ሙታ የነበረችው መላዋ ዓለም እንደገና ሕይወትን አገኘች ›› በማለት ለ፭ሺሕ ፭፻ ዘመን በመሪር መርገም ሥር ወድቃ ሕይወቷን ላጣችው ዓለም ሕይወት የኾናትን ክርስቶስን ያገኘንባት ዐዲሲቱ ሸክላ ቅድስት ድንግል መኾኗን መስክሯል፡፡
 ሊቁ ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግም በልደት ድርሳኑ ላይ ይኽነንኑ ሲመሰክር ‹‹The new pitcher of Elisha has been explained to us…›› (ዐዲሲቱ የኤልሳዕ ጋን ምሳሌነቷ ምድርን ያረጋጋች የድንግል ምሳሌ እንደኾነች ለእኛ በግልጽ ታወቀ፤ በምንጩ ውስጥ የተጨመረው ጨውም የእግዚአብሔር ልጅ ነው፤ ርሱም ባልጣፈጠው ማንነታችን ላይ ጣዕሙን የጨመረልን ነው) በማለት እመቤታችንን በማሰሮዋ፤ ጌታን ውሃውን ባጣፈጠው ጨው በመመሰል፤ በጌታ ሰው መኾን የሰው ልጆች ድኅነት እንዳገኙ በጥልቀት ተናግሯል፡፡
❖ በቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ የነገረ ማርያም አስተምህሮ ላይ ጥልቅ ጥናት ያጠናው የነገረ መለኮት ምሁሩ ጀምስ ይኽነን የቅዱስ ያዕቆብ ቃልን ሲያብራራ "The symbol of the ‘‘New pitcher of Elisha’’ is the best symbol…›" (ዐዲስቱ የኤልሳዕ ጋን ቅዱስ ያዕቆብ የድኅነትን ጭብጥ መልእክት የድኅነትን ተስፋ ካሳየባቸው ምሳሌዎች ዋነኛዋ ናት፤ የጥሩ ውሃ ዕጦትና የፍሬ የለሿ ምድር፤ ኤልሳዕ ይኽነን ተአምር እንዲሠራ ሥር መሠረቱ ነበረች፤ ይኽም ኀጢአትን የተመላ የሰዎችን ኹኔታ ይመስላል፤ በሐዲስቱ ሸክላ ያለ ይኽ ጨው የሕዝቡን ኹኔታ ለወጠ፤ ይኽም ድርጊት ወደፊት ሊመጣ ያለውን የጌታ የሰው ዘርን የማዳን ውጤትን ያሳየ ነው፤ ይኽም ምልክት ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት ያላትን ድርሻ የሚጠቁመን ነው፤ የሕዝቡን አኗኗር የለወጠው ጨው ነው፤ ግን ጨው የተቀመጠው በዐዲስ ሸክላ ነው፤ ቅዱሳት መጻሕፍት ስናነብ ክርስቶስ እኛን እንዳዳነ ይናገራል፤ ይኸውም በሐዋ ሥራ ምዕ ፬፥፲፪ ላይ ‹‹መዳንም በሌላ በማንም የለም እንድንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና›› ሲል፤ በሕዝቡ የነበረው አኗኗር ኹኔታ የተለወጠው በክርስቶስ (በጨዉ) ሲኾን፤ ማርያምም (ዐዲሲቱ ሸክላ) ለሰው ዘር ኹሉ ያንን ጨው (ጌታን) የሰጠችን (ያስገኘችልን) ናት፤ በመኾኑም ይኽ ምልክት ከድንግል ማርያም የአምላክ እናትነቷ ምስጢር ጋር የሥጋዌና የድኅነትን ምስጢር በግልጽ ያሳያል) ሲል የሰው ዘር ኹሉ ተስፋነቷንና ነገረ ክርስቶስ (Christology) ከነገረ ማርያም (Mariology) ጋር ያለውን ጥብቅ ትስስር ገልጾታል፡፡
 መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን ያጠፋ፤ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን ያደለ ጌታን የወለደችልን እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የውሃውን ምረት ያስወገደውን ጨው በያዘችው ሸክላ ብቻ ሳይኾን፤ የቅጠሉ ምረት በተወገደባት በኤልሳዕ ማድጋ ትመሰላለች (፪ነገ ፬፥፴፰-፵፩)።
 ይኸውም በዘመነ ረኀብ ደቂቀ ነቢያት ተሰብስበው ወደ ኤልሳዕ ኼዱ፤ ርሱም ደቀ መዝሙሩ ግያዝን ጠርቶ “ታላቅ ማድጋ ጥደኽ ለነቢያት ልጆች ቅጠል ለቅመኽ ቀቅለኽ ስጣቸው” አለው፤ ርሱም ክፉና በጎ ሳይለይ ለቅሞ አምጥቶ ሰጣቸው፤ እነሱም በቀመሱት ጊዜ “የእግዚአብሔር ሰው ሆይ በማድጋው ውስጥ ሞት አለ” ብለው ጮኹ፤ ከምረቱም የተነሣ መብላት ተሳናቸው፤ ኤልሳዕም “የስንዴ ዶቄት አምጥተኽ አላትነኽ ስጣቸው” አለው፤ርሱም አላትኖ ቢሰጣቸው ምረቱ ጠፍቶላቸው ጣፍጧቸው ተመግበዋል፤ ከዚኽ በኋላ በምንቸቱ ውስጥ ምሬት አልተገኘም፡፡
 ይኽም ለጊዜው ተደርጓል፤ ለኋላው ግን ምሳሌ ነው፤ ማድጋ የድንግል ማርያም፤ ቅጠል የትስብእት፤ ላተን የመለኮት፤ ምረት የፍዳ የመርገም ምሳሌ ነውና፤ ክብር ይግባውና መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን በመሻሩ ሊቃውንት ቅድስት ድንግል ማርያምን በኤልሳዕ ማድጋ መስለዋታል፤ ሊቁ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም በቊ ፴፭ ላይ ይኽነን ምስጢር በመያዝ "መስብክት ዘኤልሳዕ" (የኤልሳዕ ማድጋ አንቺ ነሽ) በማለት አመስግኗታል፡፡
 እኔም እስራኤል ኼጄ ኢያሪኮን በጐበኘኹበት ጊዜ ነቢዩ ኤልሳዕ ካጣፈጣት ጣፍጭ የበረከት ውሃ ተጠምቄ ከምንጯ በመጠጣቴ ልዩ ደስታን ኹሌ ይሰማኛልና፤ ቅዱስ ኤልሳዕን በሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም ምስጋና እንዲኽ ስል አወድሰዋለኊ፡-
“ሰላም ለኤልሳዕ ነቢይ ዘኀይለ ጸሎቱ ዐቢይ ዘዐቀመ ማየ ዮርዳኖስ ለፌ ወለፌ፤ በቅርፍተ ዕፅ እማይ ዘአውጽአ ማሕጼ፤ ዘረሰያ ለማይ መሪር ጥዕምተ፤ መዊቶሂ ዘአንሥአ በድነ ምውተ”፡፡ 
(የጸሎቱ ኀይል ደገኛ የኾነ፤ የዮርዳኖስን ወንዝ ወዲያና ወዲኽ ያቆመ፤ በዕንጨት ቅርፊትም ከውሃ ውስጥ መጥረቢያን ያወጣ፤ መሪር ውሃን ጣፋጭን ያደረገ፤ ሙቶ ስንኳ የሙቱን በድን ላነሣው ለነቢዩ ለኤልሳዕ ሰላምታ ይገባል) አሜን፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ማርያም በብሉይ ኪዳን ክፍል አንድ የሚለው መጽሐፌ
ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ
[ቅዱስ ኤልሳዕ የኢያሪኮን መራር ውሃ በጸሎቱ እንዳጣፈጠ፤ ዛሬም በምልጃው ሕይወታችንን የጣፈጠ ያድርግልን]፡፡

Tuesday, October 18, 2016

የ2009 ዓ.ም የአጽዋማትና የበዓላት አወጣጥ

በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ንዌጥን በረድኤተ እግዚአብሔር ጽሒፈ ባሕረ ቀመረ ሐሳብ ዘድሜጥሮስ ሊቀ ጳጳሳት ዘእስክንድርያ ጸሎቱ ወበረከቱ የሃሉ ምስሌነ ለዓለመ ዓለም አሜን

ይኽ መጽሐፍ መርሐ ዕውራን፤ ባሕረ ሐሳብ ይባላል፤ መርሐ ዕውራን አለው አላዋቂዎችን መርቶ ወደ ዕውቀት የሚያደርስ ስለኾነ፤ ሐሳብ ቊጥር ነው ብፁዓን እለ ተኃድገ ሎሙ ኀጢአቶሙ ወለእለ ኢኃሰበ ሎሙ ኲሎ ጌጋዮሙ እንዲል፤ ባሕረ ሐሳብ አለው ባሕር እስኪለምዱት ድረስ ያስፈራል ይገርማል፤ ከለመዱት በኋላ በልብ ተኝቶ ይውሏል ይኽም መጽሐፍ እስኪለምዱት ድረስ ያስፈራል ይገርማል ከለመዱት በኋላ ብዙ ምስጢር አስታውቆ ደስ ያሰኛልና፤ አንድም ባሕር ከለመዱት በኋላ ከመሠረቱ ወርዶ አሸዋ ይዞ ይወጧል ይኽም መጽሐፍ ከለመዱት በኋላ ብዙ ምስጢር ያስታውቃል ያስመርምራል፤ አንድም የባሕር አዟሪቱ መንገዱ ብዙ ነው የዚኽም መጽሐፍ መንገዱ ስልቱ ብዙ ነውና፤ አንድም ሐሳበ ባሕር ይላል ባሕር ዘመን ነው ሠፈራ ለባሕር በመሥፈርት ወደለዋ ለዓለም በመዳልው መኑ ዘአእመረ ስፍሐ ሰማይ ወዕመቀ ቀላይ እንዲል በባሕር ውስጥ ያለውን እግዚአብሔር እንጂ ሰው እንዳያውቀው በዘመንም ኹሉ የሚደረገውን እግዚአብሔር እንጂ ሰው አያውቀውምና፤ ኢኮነ ለክሙ ታእምሩ መዋዕለ ወአዝማነ ዘሠርዐ አብ እንዲል፡፡

ድሜጥሮስ ማለት መጽሔት ማለት ነው፤ አንድም ፀሓይ ማለት ነው ሰውን በትምህርቱ ብሩህ ያደርጋልና የድሜጥሮስ ትውልዱ ነገዱ ከአዝማደ እስክንድርያ ነው ጥንተ ነገሩ እንደምን ነው ቢሉ ያባቱ ወንድም ያጐቱ ሴት ልጅ ነበረችው አባቷ ሲሞት ልጄን ከልጅኽ አትለይብኝ አደራ ብሎት ሞተ፤ አብረው አደጉ አካለ መጠን አደረሱ ዘመኑ መናፍቃን የበዙበት ነበርና ርሱንም ከሌላ ብናጋባው ርሷንም ለሌላ ብንድራት ከሃይማኖት ይወጣሉ ከምግባር ያድጻሉ ሕንጻ ሃይማኖት ከሚፈርስ ሕንጻ ሥጋ ይፍረስ ርስ በርሳቸው እናጋባቸው ብለው መከሩ መክረው አልቀረ ሠርግ አደረጉ፤ ሥርዓተ ከብካቡ ሲፈጸም ሥርዓተ መርዓዊና ሥርዓተ መርዓት ያድርሱ ብለው ከጫጉላው ቤት አግብተዋቸው ኼዱ፡፡

ርሷን አስቀድሞ መንፈስ ቅዱስ አነሣሥቶ ድሜጥሮስ ያንት ወንድምነት ለኔ የኔ እኅትነት ላንተ አልበቃ ብሎ የባዕድ ሥራ እንሥራ አልኽን አለችው፤ እኔስ የናት ያባቴን ፈቃድ ማፍረስ ይኾንብኛል ብዬ ነው እንጂ ፈቃዴም አይደል ፈቃድሽ ካልኾነ አንተወውምን አላት እንተወው አለችው፤ እንኪያስ የተለያየን እንደኾነ አንችን ለሌላ ወንድ እኔንም ለሌላ ሴት ያጋቡናልና መስለን እንኑር አላት እንኑር አለችው፤ በአንድ ቤት በአንድ አልጋ እየተኙ 48 ዘመን ኖሩ፤ ርሱን መልአኩ ቀኝ ክንፉን ርሷን ግራ ክንፉን እያለበሳቸው ያድራል፤ ሲነጋ በመስኮቱ በአምሳለ ርግብ ወጥቶ ሲኼድ ያዩታል ስለምን ቢሉ በቅተዋልና አንድም በንጽሕናቸው ይትጉበት ብሎ፤ በዘመኑ የተሾመው ሊቀ ጳጳስ ሉክዮስ ሉክያኖስ ይባላል አረጀ ደከመ፤ ሕዝቡ ተሰብስበው አባታችን አንተ አረጀኽ ደከምኽ ካንተ ቀጥሎ የሚሾመውን ንገረን አሉት፤ እናንተም ወደ እግዚአብሔር አመልክቱ እኔም ወደ እግዚአብሔር አመለክታለኊ ብሎ ቀን ቀጥሮ ሰደዳቸው ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጣ ስሙ ድሜጥሮስ የሚባል ያለጊዜዋ ያፈራች የወይን ዘለላ ይዞ ካንተ ሊባረክ ይመጣል ካንተ ቀጥሎ የሚሾመው ርሱ ነው አለው፤ ሕዝቡም በቀጠራቸው ቀን መጡ አገኛችኹት አላቸው እኛስ አላገኘንም አሉት እኔ አገኘኹላችኊ አላቸው፤ ስሙ ድሜጥሮስ የሚባል ያለጊዜዋ ያፈራች የወይን ዘለላ ይዞ ሊባረክ ይመጣል ከኔ ቀጥሎ የሚሾመው ርሱ ነው ለጊዜው እንቢ ይላችኋል ግድ ብላችኊ ሹሙት አላቸው፡፡

ይኽም ድሜጥሮስ ተክል አጽድቆ ዕርፍ አርቆ የሚኖር ገበሬ ነበር ይላሉ፤ ከዕለታት በአንድ ቀን ተክል ለመጐብኘት ከተክል ቦታ ገብቶ ሳለ ያለጊዜዋ ያፈራች የወይን ዘለላ አገኘ ይኽንስ ከሊቀ ጳጳሱ ወስዶ ሊባረኩበት ይገባል ብሎ በንጹሕ ዕቃ አድርጎ ይዞ ኺዶ ንገሩልኝ አለ፤ እንዲኽ ያል ይዞ የመጣ ሰው ከደጅ ቁሟል ብለው ነገሩት እንዲኽ ያል ይዞ የመጣውን ከደጅ ያቆሙታልን ያገቡታልን እንጂ ግባ በለው አለው፤ ገብቶ ተባርኳል፤ ከኔ ቀጥሎ የሚሾመው ይኽ ነው ብሏቸው ወዲያው ዐረፈ፤ ቀብረው ሲመለሱ ሕዝቡ ተሾምልን አሉት በማርቆስ ወንበር የሚቀመጥ የተማረ ነው ደግሞም ንጹሕ ድንግል ነው፤ እኔ እንደምታውቁኝ ሕዝባዊ ነኝ ደግሞም ሥጋዊ ነኝ እንደምን አድርጎ ይኾናል አላቸው፤ እኛስ አባታችን ያዘዘንን ትተን ሌላ አንሾምም አሉት፤ ርሱም እንደማይተውት ዐውቆ ሊቀ ጳጳሱ ሲሾም ምን ያደርግላችኊ ነበር አላቸው አንቀጸ አባግዕን አንብቦ ይተረጒምልን ነበር አሉት ወንጌል አምጡልኝ አለ፤ አመጡለት እንኳን ትርጓሜውን ንባቡን አያውቀው የነበረ መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት ተርጒሞላቸዋል፤ ይኽም ብቻ አይደለም ብሉይና ሐዲስ ተርጒሟል፡፡

ከዚኽ በኋላ ከደጀ ሰላም ቆሞ አንተ በቅተኻል ተቀበል አንተ አልበቃኽም ቆይ እያለ ከልክሏቸዋል፤ ሕዝቡም ቆንጆ ሚስቱን ከቤቱ አስቀምጦ እኛን ይከለክለናል ብለው አምተውታል፤ መልአኩም ኢትፍቅድ አድኅኖ ርእስከ ወብእሲትከ አላ አላ አድኅኖ ሕዝብከ አለው፤ ርሱም ዕንጨት እየያዛችኊ ተሰብሰቡ ብሎ ዐዋጅ ነገረ ምእመናኑም ዕንጨት እየያዙ ተሰበሰቡ ደመራ አሠርቶ በእሳት አቃጥሎ ልብሰ ተክህኖውን ለብሶ ሊቀድስ ገባ ጸሎተ ቅዳሴውን ፈጽሞ ልብሰ ተክህኖውን እንደለበሰ በእሳቱ መኻከል እየተመላለሰ ያጥን ጀመር፤ ሚስቱም ከዚያ ነበረችና ስፍሒ አጽፈኪ ልብስሽን ዘርጊ አላት ዘረጋች እሳቱን እየታፈነ ከልብሷ ላይ አደረገላት ልብሷ ሳይቃጠል ቀርቷል ሕዝቡም አባታችን ይኽን ተአምራት ያደረግኸው ስለምን ነው አሉት፤ አምታችኹኝ አላቸው፤ አላበጀንም በድለናል ይቅር በለን አሉት፤ ይፍታሕ ወይኅድግ ያንጽሕ ወይስረይ ብሎ ናዟቸዋል፤ ኑዛዜ ከዚያ ወዲኽ ተጀምሯል፡፡
ድሜጥሮስ በተሸመ በ27 ጌታ ባረገ በ207 ዘመን ይኽን መጽሐፍ ተናግሮታል፤ ስለምን ቢሉ ከሐዋርያት ጀምሮ እስከ ርሱ የነበሩ ምእመናን ዐቢይ ጾምን የጥምቀት ሳኒታ ጀምረው በየካቲት 21 ይፈጽሙ ነበር፤ ሕማማትንም ወአጐንድዮሙ መዋዕለ ይላል በመጋቢት ያደርጉ ነበር እንዲኽ ማድረጋቸው ተጠምቆ ጹሟል ሕማሙም በመጋቢት ነው ሲሉ፤ አጽዋማትን በዓላትን እንዳገኙ ያደርጉ ነበር፤ ርሱ ግን በዘአለበዎ መንፈስ ቅዱስ ይላል ሰኞ የሚኾነውን ከሰኞ ረቡዕ የሚኾነውን ከረቡዕ ኀሙስ የሚኾነውን ከኀሙስ ዐርብ የሚኾነውን ከዐርብ እሑድ የሚኾነውን ከእሑድ እንዳይወጣ ኢየዐርግ ኢይወርድ እየሰጠ ወስኖታል፤ አይወጣም አይናወጥም ቢናወጥስ አጽዋማት በዓላትም እንደቀድሞ በኾኑ ነበር፤ ርሱም በዘአለበዎ መንፈስ ቅዱስ ባልተባለም ነበር፡፡
ድሜጥሮስ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ሐዋርያት ከሰኞ፤ ደብረ ዘይት፣ ሆሣዕና፣ ትንሣኤ፣ ጰራቅሊጦስ ከእሑድ፤ ርክብ፣ ምሕላ ድኅነት ከረቡዕ፤ ዕርገት ከኀሙስ፤ ስቅለት ከዐርብ እንዳይወጣ ግለጽልኝ ብሎ ግብር ገባ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጥቶ ከሌቱ በ23 በ23 እስከ 7 ሱባኤ ቈጥረኽ 161 ይኾናል፤ 150ውን ገድፈኽ 11 ይተርፋል፤ አበቅቴ በለው ብሎታል፤ መልአኩም ቅዱስ ሚካኤል ነው፤ ከመዓልቱም እስከ 7ት ሱባኤ ቈጥረኽ 49 ዕለት ይኾናል 30ውን ገድፈኽ 19ኝን መጥቅዕ በለው ብሎታል፤ የድሜጥስ ጥንተ አበቅቴና መጥቅዕ ይኽ ነው፡፡

የሌሊቱን አብዝቶ የቀኑን ስለምን አሳነሰው ቢሉ የሌሊት ልቡና ክት የቀን ልቡና ባካና ነውና፤ አንድም ቀን ሲፈርድ ሲተች ጉባኤ ሲያደርግ ይውላልና፤ ሕማማትን ያስቀድማል ትንሣኤን ያስከትላል ሐዘኑ ለደስታው እንዲመች፤ ካላዘኑ ደስታ ካልጾሙ ፋሲካ የለምና፤ የሐዲሱን ያስቀድማል ዘመኑ ነውና የብሉዩን ወደኋላ ያደርጋል፤ አልቦ መጥቅዕ ወአበቅቴ አንድ ወገን ያደርጋል፤ ታሪክ፣ መቅድም፣ አርዕስት እየሰጠ ወስኖታል፤ ታሪኩ ይኽ ነው፤ መቅድሙን ያመጣዋል፤ በአብ ስም አምነን አብን ወላዲ ብለን በወልድ ስም አምነን ወልድን ተወላዲ ብለን በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን መንፈስ ቅዱስን ሠራጺ ብለን ምንም ለአጠይቆ አካለት ሦስት ስላልነ በባሕርይ በሕልውና አንድ አምላክ ብለን አምነን ጸሎቱ ልመናው በረከቱ ክብሩ ይደርብንና የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ድሜጥሮስ የተናገረውን የባሕረ ሐሳብ ቊጥር መጽሐፍን በእግዚአብሔር አጋዥነት እንጀምራለን፡፡

እግዚአብሔር እንደዛሬው ኹሉ አንድነቱ ሦስትነቱን ሳይጠቀልለው ሦስትነቱ አንድነቱን ሳይከፍለው በአንድነት በሦስትነት ሳለ ክብሩ በብቻው እንደቀረ ዐውቆ ዓለምን ልፍጠር ብሎ አሰበ፤ አስቦም አልቀረ ሰውና መላእክትን ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ የቀረውን ፍጥረት ግን ለአንክሮ ለተዘክሮ ለምግበ ሥጋ ለምግበ ነፍስ ፈጠረ “ወኲሉ ዘተፈጥረ ለመፍቅደ ነባብያን ቦ እምኔሆሙ ለምህሮ ወቦ እምኔሆሙ ለተገብሮ፤ ወእንዘ ኢየኀድግ ርእሶ ዘእንበለ ሰማዕት፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘንተ እምአፍአ ብከ ሰማዕት ወመምህር ዘይመርሐከ ኀበ ዝንቱ፤ ወዘኢያስተርኢ እግዚአብሔር እምፍጥረተ ዓለም ይትዐወቅ በፍጥረቱ” እንዲል፤ እግዚአብሔርስ የፈጠረው ፍጥረት እያንዳንዱ ቢቈጠር ፍጡር ተናግሮ ባልፈጸመውም ነበር፤ እየወገን እየወገኑ ግን ብዙውን አንድ ብዙውን አንድ እያሉ ቢቈጥሩ ከእሑድ እስከ ዐርብ የፈጠረው ሥነ ፍጥረት 22 ነው፡፡ እስከዚኽ አርዕስት ነው፤ ይኽንንም በሥነ ፍጥረት ይመለከቷል፤ የፀሓይ ጥንታት ሦስት የጨረቃን ዐምስት የሚል ነውና፤ ይኽ ዓለም የተፈጠረበት ዕለተ እሑድ ጥንተ ዕለት፤ አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፀዋት የተፈጠሩበት ዕለተ ሠሉስ ጥንተ ቀመር፤ ብርሃናት የተፈጠሩበት ዕለተ ረቡዕ ጥንተ ዮን ይባላል፤ “እሑድ ወሠሉስ ወረቡዕ ዘውእቶሙ ሠለስቱ ጥንታት” እንዲል ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ዘመን ቢቈጠር በፀሓይ 7509 ዘመን፤ ከልደተ ክርስቶስ አስቀድሞ የነበረው በፀሓይ 5500 ዘመን፤ በጨረቃ 5668 ዘመን ከ10 ወር ከ9 ዕለት፤ ይኽ ዓመተ ኩነኔ፣ ዓመተ ፍዳ ይባላል፡፡ ከልደተ ክርስቶስ ወዲኽ ያለው ግን በፀሓይ 2009 ዘመን ነው ይኽ ዓመተ ሥጋዌ፣ ዓመተ ምሕረት ይባላል፤ መላው ዓመተ ዓለም ነው፤ ዓመተ ዓለም ባለው ዓመተ ምሕረት የሚል ይገኛል፤ ጊዮርጊስ ወልደ አሚድም ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት ብሎ ተርጒሞታል፤ ስለምን ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት አለው ቢሉ? ሰው በዚኽ ዓለም ሳለ ኀጢአት ሠርቶ ንስሓ ቢገባ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረት የሚያገኝበት ስለኾነ ዓመተ ዓለምን ዓመተ ምሕረት ብሎ ተርጒሞታል “በዕለት ኅሪት እሰምዐከ ወበዕለተ መድኀኒት እረድአከ ወናሁ ይእዜ ዕለት ኅሪት ወናሁ ዮም ዕለተ አድኅኖት” እንዲል፡፡

ለዚኹም መሥፈሪያ ሰባት አዕዋዳት አሉት፤ ምንና ምን ቢሉ? ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ፀሓይ፣ ዐውደ ማኅተም፣ ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡ ከሊኹም ሦስቱ በዕለት አራቱ በዓመት ይቈጠራሉ፤ በዕለት የሚቈጠሩት ሦስቱ ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት ናቸው፤ በዓመት የሚቈጠሩ አራቱ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ፀሓይ፣ ዐውደ ማኅተም፣ ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡ ዐውደ ዕለት ከእሑድ እስከ ቀዳሚት ያሉ ሰባት ዕለታት ናቸው፤ እሊኽም አውራኅን ለማስገኘት በሰባት በሰባት ሲመላለሱ ይኖራሉ “እስመ ኊልቊ ሰብአቱ በኀበ ዕብራውያን ፍጹም ውእቱ” እንዲል ዐውደ ወርኅ በፀሐይ ዘወትር ፴ በጨረቃ አንድ ጊዜ 29፤ አንድ ጊዜ ፴ ይኾናል፤ እሊኽም ዓመታትን ለማግኘት በ፴ በ፴ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡ ዐውደ ዓመት በፀሓይ 365 ዕለት በጨረቃ 354 ዕለት ነው፤ በፀሓይማ ምነው 365 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልኢት፤ በጨረቃ 354 ዕለት ከ22 ኬክሮስ ከ1 ካልዒት ከ37 ሣልሲት ከ52 ራብዒት ከ48 ኀምሲት አይደለውም ቢሉ “ወበውስተ ውሁድኒ ንብል አልቦ ወኢአሐዱ”ከ እንዲል መጽሐፍ ትርፍ ትቶ ጐደሎ መልቶ መቊጠር ልማድ ነውና ፷ ካልመላ ብሎ እንዲኽ አለ እንጂ ቊጥሩስ አለ “እስመ ልማደ መጽሐፍ ይነግር ኊልቈ ምሉዓ ወፍጹመ ወየኀድግ ዘተርፈ ወይዌስክ ዲበ ሕፀፅ ካልዐ” እንዲል፤ ዕለታትን አዕዋድ አላቸው አውራኅን የሚያስገኙ ስለኾነ፤ አውራኅን አዕዋድ አላቸው ዓመታትን የሚያስገኙ ስለኾነ “ወበከመ ይትወለዳ አውራኅ እምዕለታት ወዓመታት እምአውራኅ ከማሁ ይትወለዳ አዕምሮታት እመከራት ወእምግባራት እንዲል፡፡

ዐውደ አበቅቴ 19 ዓመት ነው በዚኽ ፀሓይና ጨረቃ መንገዳቸውን ፈጽመው በተፈጠሩበት ኆኅት ይገናኙበታል፤ ሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ መምህራነ ወንጌል ሐዋርያት፣ ሊቀ ጳጳሳት ዲሜጥሮስ ከ፳ው አንድ ቀመር አንድ ተረፈ ቀመር፤ ከ፵ው ኹለት ቀመር ኹለት ተረፈ ቀመር፤ ከ፷ው 3 ቀመር 3ት ተረፈ ቀመር፤ ከ፹ው 4 ቀመር 4ት ተረፈ ቀመር፤ ከ፻ው 5ቀመር 5ት ተረፈ ቀመር እያላችኊ ቊጠሩ ማለታቸው ከዚኽ የተነሣ ነው “ወእምዘተርፈከ እምዐሠርቱ ወተሰዓቱ ተአትት እምኔሁ አሐደ ዓመተ እስመ ለዛቲኒ ዐሠርቱ ወተሰዓቱ ሙሴ ገብራ በጥበበ እግዚአብሔር ዘይገብሩ ባቲ ፍሥሐ አይሁድኒ ወክርስቲያንኒ” እንዲል
ዐውደ ፀሓይ 28 ዓመት ነው፤ በዚኽ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፤ ዕለቱ ረቡዕ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ነው፤ ረቡዕ ማቴዎስ እንዲል፤ ዕለትን ፀሓይ አለው “ወበትእዛዝከ ይቀውም ዕለት” እንዲል፤ ወንጌላዊዉን ፀሓይ አለው “አንትሙ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም” ካለው አንዱ ርሱ ነውና፤ በሰንጠረዥ ፀ፣ ደ ይላል፤ ዐውደ ፀሓይ ማለት ነው፡፡

ዐውደ ማኅተም 76 ዘመን ነው፤ በዚኽ አበቅቴ ወንጌላዊ ይገናኙበታል፤ አበቅቴው 18 ወንጌላዊዉ ዮሐንስ ነው፤ ማኅተም አለው አበቅቴው ለአበቅቴ ወንጌላዊዉ ለወንጌላዊው ፍጻሜ ነውና፡፡ ዐውደ ቀመር 532 ዘመን ነው፤ በዚኽ ዕለት፣ ወንጌላዊ፣ አበቅቴ እሊኽ 3ቱ ይገናኙበታል፤ ዕለቱ ሠሉስ፣ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ነው፤ ሠሉስ ማቴዎስ እንዲል አበቅቴው አልቦ ነው “ጥንቱ ለቀመር ዕለተ ሠሉስ ወንጌላዊ ማቴዎስ ወፍጻሜሁ ዕለተ ሰኑይ ወንጌላዊ ዮሐንስ” እንዲል፤ በዐውደ ፀሓይ ቦታ ዐውደ ማኅተም፤ በዐውደ ማኅተም ቦታ ዐውደ ፀሓይ የሚል ይገኛል፤ ከኹለቱ አንዱ ቢታጣ አንዱ ከቀመር ገብቶ ይቈጠራል፤ ቀመርን ለሦስቱ ስም በሰጡ ጊዜ ዐውደ ቀመር ዐቢይ ቀመር፤ ዐውደ ማኅተም ማዕከላዊ ቀመር፤ ዐውደ አበቅቴ ንዑስ ቀመር ይባላል፤ ዐቢይ ቀመር መደቡ 14 ቊጥሩ 532፣532፤ ማዕከላዊ ቀመር መደቡ 6 ቊጥሩ 76፣76፤ ንዑስ ቀመር መደቡ 3 ቊጥሩ 19፣19 ነው፡፡

ከዚኽም ዓመተ አበቅቴን ለማግኘት 7509 ዘመን በዐቢይ ቀመር ቢቀምሩ 532፤ 532 የተፈጸመለት 14 ዐቢይ ቀመር፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኾኖ 4 ዓመት ይተርፋል፡፡

መላውንም በማእከላዊ ቀመርም ቢቀምሩ 76፤ 76 የተፈጸመለት 98 ማእከላዊ ቀመር 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኹኖ 4 ዓመት ይተርፋል፡፡

በዐውደ ፀሓይም ቢቀምሩ 28፤ 28 የተፈጸመለት 266 ዐውደ ፀሓይ፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 3 ንዑስ ቀመር ኾኖ 4 ዓመት ይተርፋል፡፡

መላውንም በንዑስ ቀመር ቢቀምሩ 19፤ 19 የተፈጸመለት 395 ንዑስ ቀመር ኹኖ 4 ዓመት ይተርፋል፡፡

7509ኙን ዘመን በቀመረ ዐረብም ቢቀምሩ 228፤ 228 የተፈጸመለት 32 ቀመረ ዐረብ፤ 19፤ 19 የተፈጸመለት 11 ንዑስ ቀመር ኹኖ 4 ዓመት ይተርፋል፤ ስመ አቅማር ብዙ ነው አይቶ መተው ነው፤ አሐደ አዕትት ለዘመን እንዲል ስለተጀመረ ተቈጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ ብሎ ከ4ቱ አንዱን ቢያትቱ 3 ይተርፋል፤ 3 ዓመተ አበቅቴ ወጣ ገጠር ወንበር ይላል፤ አበቅቴን ለማግኘት ከ3ቱ ዓመተ አበቅቴ 11፤ 33 ይኾናል፤ ፴ውን ቢገድፉት 3 ይተርፋል፤ 3 አበቅቴ ወጣ በዘመነ ማቴዎስ፡፡

መጥቅዕንም ለማግኘት ከ3ቱ ዓመተ አበቅቴ 19 ዕለት ቢነሡ 57 ይኾናል፤ 30ውን በ1 ሱባኤ ቢገድፉት 27 ይቀራል፤ 27 መጥቅዕ ወጣ በዘመነ ማቴዎስ፤ 3ት አበቅቴ እና 27 መጥቅዕ ፴ ይኾናሉ እንጂ ከ፴ አይወጡም ከ፴ አይወርዱም፤ “ዓዲ መጥቅዕ ወአበቅቴ ክልኤሆሙ እመ ይበዝኁ ወእመ ይውኅዱ ኢየዐርጉ እም፴ ወኢይወርዱ እም፴ ወባሕቱ ወትረ ይከውኑ ፴” እንዲል
(ከዚኽ በኋላ አበቅቴ ከመጠነ ሠርቀ መዓልትና ከሚለው ዠምሮ…ኢየዐርግ ኢይወርድ ኹሉ እንደ ታሪኩ አስገባ)
ከዚኽም በዘመኑ የኾኑ አጽዋማትና በዓላትን ይናገሯል፤

መጥቅዕ 27 መጥቅዕ ቢበዛ በመስከረም ይውላልና መስከረም እሑድ ይብታል፤ ከእሑድ እስከ እሑድ 8፤ ከእሑድ እስከ እሑድ 15፤ ከእሑድ እስከ እሑድ 22፤ ሰኞ 23፤ ማግሰኞ 24፤ ረቡዕ 25፤ ኀሙስ 26፤ ዐርብ 27 በዐለ መጥቅዕ መስከረም 27 ዐርብ ቀን ይውላል፤ የዐርብ ተውሳክ 2፤ 2ና27= 29 መባጃ ሐመር ይገኛል፤ በመስከረም ሳኒታ ጥር ሰኞ ይብታል፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 8፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 15፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 22፤ ሰኞ እስከ ሰኞ 29፤ ጥር 29 ነነዌ ይውላል፡፡

የዐቢይ ጾም ተውሳክ 14፤ 14ና29=43፤ ፴ውን ገድፎ 13 ይቀራል፤ የካቲት ረቡዕ ይብታል፤ ረቡዕ እስከ ረቡዕ 8፤ ኀሙስ 9፤ ዐርብ 10፤ ቅዳሜ 11፤ እሑድ 12፤ ሰኞ 13 የካቲት 13 ቀን ዐቢይ ጾም፡፡
የደብረ ዘይት ተውሳክ 11፤ 11 ና 29=40፤ ፴ውን ገድፎ 10 ይቀራል፤ መጋቢት ዐርብ ይብታል፤ ዐርብ እስከ ዐርብ 8፤ ቅዳሜ 9፤ እሑድ 10፤ መጋቢት 10 ቀን ደብረ ዘይት
የሆሳእና ተውሳክ 2፤ 2ና 29=31፤ ፴ውን ገድፎ 1 ይቀራል፤ ሚያዝያ እሑድ ይብታል፤ ሚያዝያ 1 ሆሳዕና
የስቅለት ተውሳክ 7፤ 7 ና 29=36፤ ፴ውን ገድፎ 6 ይተርፋል፤ እሑድ 1፤ ሰኞ 2፤ ማግሰኞ 3፤ ረቡዕ 4፤ ኀሙስ 5፤ ዐርብ 6፤ ሚያዝያ 6 ስቅለት ይተርፋል፡፡
የትንሣኤ ተውሳክ 9፤ 9 ና 29= 38፤ ፴ውን ገድፎ 8 ይተርፋል፤ እሑድ እስከ እሑድ 8፤ ሚያዝያ 8 ትንሣኤ
የርክብ ተውሳክ 3፤ 3 ና 29=32፤ ፴ውን ገድፎ 2 ይተርፋል፤ ግንቦት ማግሰኞ ይብታል፤ ማግሰኞ 1፤ ረቡዕ 2፤ ግንቦት 2 ርክበ ካህናት
የዕርገት ተውሳክ 18፤ 18ና 29=47፤ ፴ውን ገድፎ 17 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 15፤ ረቡዕ 16፤ ኀሙስ 17፤ ግንቦት 17 ዕርገት
የጰራቅሊጦስ ተውሳክ 28፤ 28 ና 29=57፤ ፴ውን ገድፎ 27 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 15፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 22፤ ረቡዕ 23፤ ኀሙስ 24፤ ዐርብ 25፤ ቅዳሜ 26፤ እሑድ 27፤ ግንቦት 27 በዓለ ጰራቅሊጦስ፡፡
የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ 29፤ 29 ና 29=58፤ ፴ውን ገድፎ 28 ይቀራል፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 15፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 22፤ ማግሰኞ እስከ ሰኞ 28፤ ግንቦት 28 ጾመ ሐዋርያት፡፡
የምሕላ ድኅነት ተውሳክ 1፤ 1 ና 29= 30፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 8፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 15፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 22፤ ማግሰኞ እስከ ማግሰኞ 28፤ ረቡዕ 30፤ ግንቦት 30 ምሕላ ድኅነት ይውላል፡፡

ዓመተ ወንጌላዊን ከዚኽ ይናገሯል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዓመተ ወንጌላዊ ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ ለእመ ተርፈ አሐዱ ማቴዎስ ወክልኤቱ ማርቆስ ወሠለስቱ ሉቃስ ወለእመ ዐረየ ክፍል ዮሐንስ እንዲል፤ ዓመተ ወንጌላዊን ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ አንድ ቢተርፍ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ መኾኑ፤ ኹለት ቢተርፍ ማርቆስ፤ ሦስት ቢተርፍ ሉቃስ ቢተካከል መኾኑን በዚኽ ይታወቃል፤ 7509 ዘመን ለአራቱ ወንጌላውያን ቢያካፍሉ 1878 ደርሷቸው 1 ይተርፋል፤ 1 ቢተርፍ ማቴዎስ ያለው ይኽ ነው፤ ዛሬ ወንጌላዊዉ ማቴዎስ መኾኑ በዚኽ ታውቋል፡፡

ጥንተ ዮንንም ከዚኽ ይናገሯል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ጥንተ ዮን ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ ወትዌስክ ቦቱ መጠነ ራብዒት ወትገድፎ በበሱባኤ ወዘተርፈከ እምሱባኤ ተአትት እምኔሁ አሐደ ዓመተ ወእምዝ ይከውን ጥንተ ዮን እንዲል፤ ጥንተ ዮንንም ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ 5ኛ መጠነ ራብዒት 6ኛ ጳጉሜንን አክሎ በሱባዔ ገድፎ ከሱባዔ የተረፈውን አንዱን አትቶ 1 ቢተርፍ ጥንተ ዮን ረቡዕ መኾኑን መስከረም ረቡዕ መባቱን፤ 2ት ቢተርፍ ኀሙስ፤ 3 ቢተርፍ ዐርብ፤ 4 ቢተርፍ ቀዳሚት፤ 5 ቢተርፍ እሑድ፤ 6 ቢተርፍ ሰኞ፤ 7 ቢተርፍ ማግሰኞ መኾኑ በዚኽ ይታወቃል፡፡ አከፋፈል እንዳለፈው፤ ይታወቃል፤ 7509 ዘመን ለአራቱ ወንጌላውያን ቢያካፍሉ 1878 ደርሷቸው 1 ይተርፋል፤ ይኽን በሱባዔ ይገድፏል፤ ከሺው 300 ነሥቶ 700 ግዱፍ፤ ከ800ው አንዱን መቶ ነሥቶ 700 ግዱፍ፤ 400 ይተርል፤ ከ100ው 2፤ ከ400ው 8፤ ከ8ቱ አንድ፤ ከዚያም 1 እና 78= 79 ይኾናል፤ ከ79ኙ 70ውን በ11 ሱባዔ ቢገድፉ 2 ይተርፋል፡፡

ከአንዱ ወንጌላዊ 2 ከ4ቱ ወንጌላውያን 8፤ መጠነ ራብዒት፤ 6ኛ ጳጉሜን 1878 ዕለት ትኾናለች፤ ርሷ በዕለት፤ ወንጌላዊ በዓመት ይተካከላሉና ግድፈት እንዳለፈው፤ መጠነ ራብዒት 2= 12፤ ከዓመተ ወንጌላዊ የተረፈ 1 ና 12= 13 ይኾናል፤ ከ13ቱ 7ቱን በአንድ ሱባዔ ቢገድፉ 6 ይተርፋል፤ አሐደ አዕትት ለዘመን እንዲል ስለተዠመረ ተቈጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ ብሎ ከ6ቱ አንዱን ቢያትቱ 5 ይተርፋል፤ 5 ቢተርፍ እሑድ ያለው ይኽ ነው፤ የእሑድ ጥንተ ዮን 5 ነውና፡፡ ጥንተ ዮንም ማለት ጥንተ ፀሓይ፤ ጥንተ ጨረቃ፤ ጥንተ ከዋክብት ማለት ነው፤ ጥንተ ዮን ብሂል ጥንተ ተፈጥሮቶሙ ለፀሓይ፤ ወወርኅ ወከዋክብት እንዲል፡፡
ዕለተ ቀመርንም ለማወቅ ለጥንተ ዮን ከወጣው አንዱን ሳያትቱ በሱባዔ ገድፎ 1 ቢተርፍ ማግሰኞ መኾኑ፤ 2 ቢተርፍ ረቡዕ፤ 3 ቢተርፍ ኀሙስ፤ 4 ቢተርፍ ዐርብ፤ 5 ቢተርፍ ቀዳሚት፤ 6 ቢተርፍ እሑድ፤ 7 ቢተርፍ ሰኞ መኾኑ በዚኽ ይታወቃል፤ ለጥንተ ዮን የወጣው 6 ነው፤ 6 ቢተርፍ እሑድ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ቀመርም ማለት ቀመር የተዠመረበት ዕለት ማለት ነው፤ ቀመር የተዠመረው ማግሰኞ ነውና፡፡

ዕለተ ዮሐንስንም ከዚኽ ይናገሩታል፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዕለተ ዮሐንስ ትከፍሎ ለዘመን ኀበ አርባዕቱ እድ፤ ወትዌስክ ቦቱ መጠነ ራብዒት፤ ወክልዔተ ዕለተ ጠቢባን ወትገድፎ በበሱባዔ ወዘተርፈከ እምሱባዔ ኢተአትት አሐደ ዓመተ፤ ወእምዝ ይከውን ዕለተ ዮሐንስ እንዲል ዕለተ ዮሐንስን ለማወቅ ዓመተ ዓለምን ከአራት ከፍሎ፤ 5ኛ መጠነ ራብዒት፤ 6ኛ ጳጉሜንን አክሎ 7ኛ 2ት ዕለተ ጠቢባንን ጨምሮ በሱባዔ ገድፎ ከሱባዔ የተረፈውን አንዱን ሳያትቱ አንድ ቢተርፍ ዕለተ ዮሐንስ እሑድ መኾኑ፤ 2 ቢተርፍ ሰኞ፤ 3 ቢተርፍ ማግሰኞ፤ 4 ቢተርፍ ረቡዕ፤ 5 ቢተርፍ ኀሙስ፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ፤ 7 ቢተርፍ ቀዳሚት መኾኑ በዚኽ ይታወቃል ለጥንተ ዮን የወጣ 6 እና 2 ዕለተ ጠቢባን= 8 ሱባዔውን ቢገድፉ 1 ይተርፋል፤ 1 ቢተርፍ እሑድ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ዮሐንስም ማለት አሻቅቦ ወደ ላይ እስከ ፍጥረተ ዓለም፤ አቈልቊሎ ወደ ታች እስከ ምጽአተ ክርስቶስ ቢቈጥሩ ለወንጌላዊዉ ዮሐንስ የሚደርሰው ቀን ማለት ነው፤ ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘኀለፈ ይመርሐከ ዝንቱ እስከ ፍጥረተ ዓለም ወለእመ ፈቀድከ ታእምር ዘይመጽእ ያበጽሐከ ዝንቱ እስከ ምጽአተ ክርስቶስ እንዲል፤ አንድም ሠርቀ ቲቶን ዕለተ ዮሐንስ ይለዋል፤ ቲቶ የተባለው መስከረም ነው፤ የመጥምቁ ዮሐንስ በዓል የሚውልበት ቀን ማለት ነው፤ ርዕሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ እንዲል፡፡

ዕለተ በዓል ዘኀለፈ ዕለተ በዓል ዘይመጽእ የእሑድ አሚሩ ሰንበተ ክርስቲያንን ለማወቅ በዘመኑ የወጣውን ጥንተ ዮን፤ ሠርቀ መዓልት፤ 2 ዕለተ ጠቢባን በየወሩ የሚገኘውን አጽፈ ወርኅ እሊኽን 4ቱን አንድ አድርጎ ቈጥሮ በሱባዔ ገድፎ 1 ቢተርፍ እሑድ አሚሩ፤ 2 ቢተርፍ ሰኞ ሰኑዩ፤ 3 ቢተርፍ ማግሰኞ ሠሉሱ፤ 4 ቢተርፍ ረቡዕ ረቡዑ፤ 5 ቢተርፍ ኀሙስ ኀሙሱ፤ 6 ቢተርፍ ዐርብ ሰዱሱ፤ 7 ቢተርፍ ቀዳሚት ሰቡዑ፤ 8 ቢተርፍ በሱባዔ ገድፎ እሑድ አሚሩ የሚያሰኘው ይኽ ነው፡፡ አጽፈ ወርኅም ማለት የወርኁ ከወርኅ የሚደረብ ማለት ነው፤ ይኽስ ከምን ይገኛል ቢሉ? ወሩን በሱባዔ ቢገድፉ 4 ሱባዔ ኾኖ 2 ይተርፋል፤ የወርኁ 2 የዓመቱ 24፤ እንዲኽ ግን ስለኾነ ለመስከረም አጽፈ ወርኅ የለውም በጥንተ ዮን፤ በሠርቀ መዐልት በኹለት ዕለተ ጠቢባን ይቈጠራል፤ በእሊኽ በ3ቱ ይቈጠራል፤ ጥንተ ዮን 5፤ ሠርቀ መዐልት 1=6፤ ኹለት ዕለተ ጠቢባን 8 ይኾናል፤ በሱባኤ ሲገድፉ 1 ይተርፋል፤ 1 ቢተርፍ እሑድ አሚሩ ያለው ይኽ ነው፤ ዕለተ ጠቢባንም ማለት ጠቢባን ሥላሴ ይኽነን ዓለም የፈጠሩበት፤ ጠቢባን መላእክት ሥላሴን የሚያመሰግኑበት ቀን ማለት ነው፤ (ዬ) ጠቢባን ሥላሴ ይኽነን ዓለም ከእሑድ እስከ ዐርብ ፈጥረዋል፤ ጠቢባን መላእክት ሥላሴን ዘወትር ያመሰግናሉ ብሎ የቊጥር መጽሐፍን የተማሩ መምህራን ዕለተ ሰንበትን፤ 6ቱ ዕለታትን፤ ያለፉትን የሚመጡትን በዓላት የሚያውቁባቸው የሚያሳውቁባቸው ማለት ነው፤ ዕለተ ጠቢባንም የተባሉ እሑድና ሰኞ ናቸው፤ ከቀመር ገብተው አልተቈጠሩም፡፡

ዕለተ ምርያ አዕዋዲትንም ለማወቅ የፀሓይ ዐውደ ዓመት 365 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ነው፤ ይኽነን በሱባዔ ቢገድፉት 52 ሱባዔ ኾኖ 1 ዕለት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ይተርፋል፤ ይኽቺውም አንድ ዕለት የተባለችው ዐምስተኛዪቱ ጳጒሜን ናት፤ ዕለተ ምርያ አዕዋዲት ይላታል፤ ዕለተ ምርያ ማለት ዕለተ መድኀኒት ማለት ነው፤ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበትን ቀን የምታሳውቅ ማለት ነው፤ ርሷ በዋለች ልደት ይውላልና፤ አዕዋዲትም አላት ዘመኑን የምታዘዋውር የምታለዋውጥ ማለት ነው፤ እሑድ የዋለውን ሰኞ፤ ሰኞ የዋለውን ማግሰኞ እንዲውል የምታደርግ ርሷ ናትና፡፡

መጠነ ራብዒት 6ኛ ጳጉሜንም ለማወቅ የአንዱ ዓመት ኬክሮስ 15፤ የ2 ዓመቱ 30፤ የ4 ዓመቱ 60 ኬክሮስ ነው፤ 60ው ኬክሮስ 1 ዕለት ይኾናል፤ ይኽቺውም በሉቃስ መጨረሻ ዮሐንስን ተጠግታ የምትውል ስድስተኛዪቱ ጳጉሜን ናት፤ መጠነ ራብዒት፣ ሠግረ ዮሐንስ ይላታል፤ መጠነ ራብዒት አላት ርሷ በዕለት ወንጌላዊ በዓመት ይተካከላሉና፤ ሠግረ ዮሐንስም አላት ዮሐንስ ተራምዶ የሚውልባት ስለኾነ፡፡

ዕሪና መዓልትና ዕሪና ሌሊትንም ለማወቅ የአንዱ ዓመት ካልዒት 6፤ የ5ቱ ዓመት 30፤ የ10ሩ ዓመት 60 ይኾናል፤ 60ው ካልዒት 1 ኬክሮስ ይኾናል፤ የ100ው ዓመት 10 ኬክሮስ፤ የ600 ዓመት 60 ኬክሮስ፤ 60ው ኬክሮስ አንድ ዕለት ይኾናል፤ ይኽቺውም ሰባተኛዪቱ ጳጉሜን ናት፤ ዓለም በተፈጠረ በ600 ዘመን ዕሪና መዓልት ዕሪና ሌሊት ኾኗል፤ ዓለም ከተፈጠረ ዠምሮ እስከ ዛሬ ድረስ 12 ዕሪና መዓልት 12 ዕሪና ሌሊት ኾኖ 13ኛው ከተዠመረ 309 ኾኖ በዘመነ ማቴዎስ ይኸውም ሊመላ 291 ይቀራል፡፡
ከዚኽ በኋላ እንዲኽ ብሎ ባሕረ ሐሳብ አውጪው አሥርቆት ያውጣ፡፡

በዘንዜከር ሐሳባተ ሕጉ ወትእዛዙ ለእግዚእነ ወአምላክነ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዘ ሀሎነ በዘመነ ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ዘመነ ማርቆስ ዜናዊ፤ ወንጌላዊ አለው ማቴዎስን ባለዘመን ነውና፤ ዜናዊ አለው ማርቆስን የሚመጣ ነውና ወረኛ ንጉሥ እንዲሉ፡፡ በሰብዐ ወኀምስቱ ምእት ወተሱዑ ዓመተ ዓለም፡፡ በኀምሳ ወኀምስቱ ምዕት ዓመተ ኩነኔ፤ በዕሥራ ምዕት ወተሱዑ ዓመተ ምሕረት፤ ሠረቀ ለነ ወርኀ መስከረም ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ወርኀ ጥቅምት በሰላመ እግዚአብሔር አሜን፤ አበቅቴ 3 ሠርቀ መዓልት 1፤ ሕጸጽ 1= 5 ኀሙሱ ሠርቀ ሌሊት፤ ተሱዑ ሠርቀ ወርኅ፤ አሚሩ ሠርቀ መዓልት፤ አሚሩ ሠርቀ ዕለት፤ ዮም በዛቲ ዕለት ዘአቅረብነ ለከ አምኀ ስብሐት ያዐርጉ ለነ መላእክት ተወከፍ ለነ እግዚአ ስብሐት፤ ወስብሐት ለእግዚአብሔር
አዘጋጅ፡- መጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ

Friday, August 21, 2015

ስለ እመቤታችን ዕረፍትና ዕርገት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን 
 
ነሐሴ 16-የብርሃን እናቱ የሆነች የወላዲተ አምላክ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋዋ በክብር ወደ ሰማይ ያረገበት ዕለት ነው፡፡ ዳግመኛም ዛሬ የሰማዕቱ የቅዱስ ጊጋር በዓለ ዕረፍቱና ፍልሠተ ሥጋው ነው፡፡ ይኸውም ቅዱስ ጊጋር የደቡብ ሶሪያ መስፍን ሲሆን እመቤታችንና ልጇን መድኀኔዓለምን እነ ዮሴፍንም አብሮ ወደቤቱ አስገብቶ በመደበቅ ከሄሮድስ ጭፍሮች ያዳናቸው ነው፣ ይህንንም በማድረጉ የተሰየፈ ሰማዕት ነው፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ "ቀዳሜ ሰማዕት" መሰኘቱ ከጌታችን ሞት ቀጥሎ እርሱ ሰማዕት በመሆኑ ነው እንጂ በሐዲስ ኪዳን በመጀመሪያ ሰማዕት በመሆንስ እነ መጥምቁ ዮሐንስና እነ ቅዱስ ጊጋር ይቀድሙታል፡፡ ይኸውም ቅዱስ ጊጋር የደቡባዊ ሶርያ መስፍን ነበር፡፡ እመቤታችን ልጇን መድኃኔዓለምን ይዛ ወደ ግብፅ ስትሰደድ የሄሮድስ ጭፍሮች እመንገድ ላይ ስለደረሱባቸው ቅዱስ ጊጋር እመቤታችንና ልጇን መድኀኔዓለምን እነ ዮሴፍንም አብሮ ወደቤቱ አስገብቶ ደብቋቸው በሄሮድስ ጭፍሮች ከመ
ሞት አድኗቸዋል፡፡ ቅዱስ ጊጋርም እመቤታችንና ልጇን መድኀኔዓለምን በሄሮድስ ጭፍሮች ከመሞት ካዳናቸው በኋላ ሸኝቷቸዋል፡፡ ቀጥሎም የራሱን ወታደሮች ሰጥቷቸው ረጅም መንገድ እንዲሸኟቸው አድርጓል፡፡ ሄሮድስም ይህን ሲሰማ ጭፍሮቹን ልኮ ቅዱስ ጊጋርን ካስመጣው በኋላ ከብረት ጋር አስሮ 40 ቀን እጅግ አድርጎ አሠቃየው፡፡ አካሉንም ከሦስት ቦታ እየቆራጠ ካሠቃየው በኋላ ነሐሴ 16 ቀን አንገቱን በሰይፍ አስቆርጦታል፡፡ ጌታችንም ለቅዱስ ጊጋር ተገልጦለት ሦስት የክብር አክሊላትንና ሌላም አስደናቂ የድኅነት ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡ የቅዱስ ጊጋር በረከቱ ይደርብን!!!
 
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዕርገት
   
ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ 

 
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዕርገት
 
 (ከዚህ ቀጥሎ ያለው ሙሉው ጽሑፍ የመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ ነው፡፡) ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ ስለ እመቤታችን ዕረፍትና ዕርገት ቊጥሩ ከ72ቱ አርድዕት አንዱ የሚኾነው ቅዱስ ኢቮዲየስ ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር ስለነበረ በጥር ፳፩ የኾነ የቅድስት ድንግል ማርያም ዕረፍትና በነሐሴ ፲፮ የተከናወነ በዓለ ዕርገቷን በዐይኖቹ የተመለከተውን “የቅድስት ድንግል ማርያም ኅልፈተ ሕይወትና ፍልሰት” በሚል ርዕስ ጽፏል፤ በዐይኑ አይቶ የጻፈውን ይኽነንም የቅድስት ድንግል ማርያምን የዕረፍቷና የዕርገቷ ታሪክ “ነገረ ማርያም በሊቃውንት ክፍል አንድ” በሚለው መጽሐፌ ላይ የጻፉኩት ሲሆን፤ ብዙዎቻችሁ መጽሐፉ አላችሁ፤ ግን መጽሐፉን ማግኘት ያልቻሉ በሌላ ሀገር ላሉት ጓደኞቼ በጥቂቱ ጽፌላችኋለኹና እነሆ፡- “ድርሳን ዘደረሰ አባ ኢቮዲየስ ሊቀ ጳጳሳት ዘአንጾኪያ በእንተ ዕረፍታ ወፍልሰታ ለማርያም” Evodius of Rome, Homily on the Dormition The falling asleep of Mary “An instruction which our holy and in every wise honourable father Abba Evodius, the archbishop of the great city Rome, who was the second after Peter the apostle,…” (የእኛ ቅዱስ እና በማናቸውም ረገድ ብልኅ እና የተከበረ አባታችን፣ የታላቋ የሮም ከተማ ሊቀ ጳጳስ፣ ከሐዋርያው ጴጥሮስ በኋላ ኹለተኛው በኾነው የቀረበ መመሪያ፡፡ የኹላችንም እመቤት፣ እግዚአብሔርን የተሸከመች ቅድስት ማርያምን አስመልክቶ፤ በእግዚአብሔር ሰላም በግብጻውያን አቈጣጠር በ፳፩ኛው የጦቢ (ጥር) ወር ቅዱስ ሕይወቷን ያበቃችውን እመቤታችን አስመልክቶ የቀረበልን አስተምህሮ አሜን)፡፡
፯. “Now it came to pass at the hour of the light on the twenty-first of the month Tobi, …” (በጦቢ ወር በ፳፩ በብርሃን ሰዓት ላይ በነጋታው፣ እውነተኛው ቃል ክርስቶስ በኪሩቤል ሠረገላው ላይ ተቀምጦ እልፍ አእላፋት የሚቈጠሩ መላእክት ተከትለውት፣ በዙሪያው የብርሃን ኀይሎች ከብበውት እና ዳዊት በእሳት ሠረገላ ላይ ኾኖ ከፊቱ እየዘመረለት፣ መንፈሳዊ በገናን እየተመታ ከፍ ባለ ድምፅ ለኀያሉ ጌታችን ክብር እንዘምርለት አለ፡፡ መድኀኒታችን በመኻከላችን ቆመ፣ በሮቹ ተዘጉ ወደ ኹላችንም እጆቹን ዘረጋቸው፤ ብዙዎች ደቀ መዛሙርት በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፤ ሰላም ለእናንተ ይኹን አለን፡፡ ኹላችንም በአንድ ላይ ተነሥተን እግሮቹ ሥር ወድቀን የአምልኮት ምስጋናን አቀረብንለት፤ ርሱም በሰማያዊዉ በረከቱ ባረከን፡፡ መላእክቱም አሜን ብለው መለሱ፤ ርሱም ወደ አባቴ ጴጥሮስ በመዞር “በረከት ልሰጣችኊ በመኾኑ መሠዊያዉን ጠብቀው” አለው፤ “በዛሬው ቀን ከእናንተ መኻከል ታላቅ ስጦታ ማግኘት አለብኝ” አለ፡፡ እኛ ግን በእግሮቹ ላይ ተደፍተን አመለክነው እኛም “ከእናንተ መኻከል በዛሬው ዕለት ታላቅ ስጦታ ለመውሰድ እፈልጋለኊ ስትል ምን ማለትኽ ነው” ብለን አጥብቀን ለመንነው፡፡ መድኀኒታችንም ሲመልስልን “ከዓለም ኹሉ አብልጬ የመረጥኋችኊ ክቡራን ኅዋሶቼ ይኽቺ ቀን የአባቴ ዳዊት ትንቢት የሚፈጸምባት ቀን ናት፣ ንግሥቷ በወርቅ በተንቆጠቆጠ አልባሷ አጊጣ እና አሸብርቃ በቀኜ ትቆማለች (መዝ ፵፬፥፱)፡፡ ዛሬ ለዘጠኝ ወራት በምድር ላይ መኖሪያዬ ኾና የቆየችውን ድንግል እናቴን የምቀበልበት እና ከእኔ ጋር ወደ ሰማያት ሰማያዊ ቦታዎች ይዤያት በመውሰድ ለመልካሙ አባቴ በስጦታ የማስረክባት ቀን ነው፣ ዳዊትም እንኳን “በኋላዋ ደናግሉን ለንጉሥ ይወስዳሉ፤ ባልንጀሮችዋንም ወደ አንተ ያቀርባሉ” (መዝ ፵፬፥፲፬) እንዳለ፤ ርሱም በመለኮታዊዉ እና ግሩም ድምፁ የኔ ውድ እናት ሆይ ተነሥተሽ ወደ እኔ ነዪ (መሓ ፪፥፲)፤ የነፍሴ ደስታ የኾንሽ ወደ እኔ ነዪ (መሓ፪፥፲፫) አላት፤ አንቺ ከቄዳር ልጆችም በላይ ውብ ቆንዦ ነሽ (መሓ ፩፥፭)፤ አንቺ የተመረጥሽ ጎጆ ሆይ የመልካማ ርግብ መኖርያ ነሽ፤ አንቺ የተመረጥሽ የአትክልት ስፍራ ያለምንም ዘር እና የወንድ ሩካቤ መልካሙን ፍሬ ያፈራሽ (መሓ ፬፥፲፪)፤ አንቺ የወርቅ መሶብ ሆይ መናው እውነተኛው መና እኔ እንኳን የተሰወርኹብሽ (ዘፀ ፲፮፥፴፫-፴፬)፤ አንቺ ስዉር ቅርስ እውነተኛው ብርሃን የተሰወረብሽ እና ከአንቺም ውስጥ ወጥቶ በመገለጽ በሰው ልጆች ላይ የተትረፈረፈ ሀብት ያስገኘላቸው፡፡ ተነሥተሽ ወደ እኔ ነዪ የእኔ ውብ ርግብ ሆይ (መሓ ፮፥፱) የእኔ ቅድስት መርዐት (መሓ ፬፥፰)፣ የእኔ ንጽሕት መስክ፣ ከእኔ ጋር ወደ አትክልት ስፍራው እወስድሻለኊ (መዝ ፸፩፥፮) ከርቤ እና ጣፋጭ ቅመማ ቅመሜን እደረድርልሻለኊ (መሓ ፬፥፲፬) ከበታችሽም እንድታርፊበት ያማረውን ምንጣፍ አነጥፍልሻለኊ፤ ማርያም እናቴ ሆይ አንቺ የተባረክሽ ነሽ ወደ ምድር ወልደሽ አምጥተሽኛልና፡፡ እኔ ኹሉን መጋቢ የኾንኹትን ያጠቡ ጡቶሽን የተባረኩ ናቸው፡፡ እንዲኹም በከፍታ ቦታዎች ወደሚገኙ ሰማያዊ ስፍራዎች ወስጄሽ በአባቴ በመልካም ነገሮች እመግብሻለኊ፡፡ እስከዚያው በጉልበትሽ ላይ ያስቀመጥሺኝ ድንግል እናቴ ማርያም ሆይ በኪሩቤል ሠረገላ ላይ በማኖር ከእኔና ከቸሩ አባቴ ጋር ወደ ሰማያት እወስድሻለኊ፡፡ በመጠቅለያ ጨርቆች እንደጠቀለልሽኝ ኹሉ የእኔ ድንግል እናት ማርያም ሆይ በወለድሽኝ ዕለት በከብቶች በረት ከላም እና አህያ ጋር በአንድ ላይ ከብበውኝ እንዳኖርሽኝ ኹሉ (ኢሳ ፩፥፫፤ ሉቃ ፪፥፯)፤ እኔ ደግሞ ዛሬ ከእኔ ጋር ከሰማያት ባመጣዋቸው በሰማይ መጐናጸፊያ ሰውነትሽን እጠቀልለዋለኊ፤ ከዚያም ከሕይወት ዛፍ ሥር አስቀምጠዋለኊ፣ ኪሩቤልም በሰይፈ ነበልባላቸው እንዲጠብቁት አደርጋለኊ (ዘፍ ፫፥፳፬)፡፡ የተባረከችውን ነፍስሽን የሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም መንበር በተሸፈነችበት መሸፈኛዎች እንድትሸፈን አደርጋለኊ፡፡ እኔን በሚያሳድድበት ጊዜ ሥርዓት አልባውን ሄሮድስ በመፍራት ወደ ግብጽ ምድር እንደተሰደድሽው ኹሉ (ማቴ ፪፥፲፫-፲፰)፤ መላእክቶቼ ኹልጊዜም በክንፎቻቸው እያጠሉብሽ እና መልካም ዝማሬያቸውን እንዲዘምሩልሽ አደርጋለኊ)፡፡
፰. “Now when we heard these things, as our Saviour was saying them to His virgin mother,…” (እነዚኽን ነገሮች ስንሰማ፣ መድኀኒታችን ለድንግል እናቱ እንደተናገረው፣ በሥጋ ሊወስዳት እንደፈለገ ኹላችንም ዐወቅን፡፡ ኹላችንም ፊታችንን አዙረን አምርረን አለቀስን፤ የኹላችንም እናት ቅድስት ድንግል ማርያምም ከእኛ ጋር በአንድ ላይ አለቀሰች፡፡ መድኀኒታችንም ለምን ታለቅሳላችኊ አለን? አባቴ ጴጥሮስም “ጌታዬ እና አምላኬ ሥርዓት አልበኞቹ አይሁድ አንተን በሰቀሉኽ ጊዜ በወደቀብን ከባድ ዐዘን የተነሣ ለጥቂት ቀናት አልቅሰን ነበር ግን በኋላ ላይ አንተ ከሞት በመነሣትኽ እጅግ ተደሰትን፤ አንተም ወደ እኛ ቀርበኸን በረከትኽን ለገስኸን፤ በሥጋ የአንተ እናት ብትኾንም የኹላችንም እናት ለኾነችው ወደ ድንግል እናትኽ ማርያም አደራ ጣልኽብን፡፡ አኹን ግን ርሷን ከእኛ የምትወስድብን ከኾነ የሚወድቅብንን ከባድ ዐዘን ለመቋቋም ስለማንችል ርሷን ከመውሰድኽ በፊት እኛኑ አስቀድመን” አለው፡፡ መድኀኔ ዓለምም “የእኔ የተመረጥኽ ጴጥሮስና በእኔ የተመረጣችኊ ሐዋርያቶች ሆይ በሙሉ ትቼያችኊ (ተለይቼያችኊ) እንደማልቀር እና ተመልሼ እንደምመጣ አልነገርኋችኹምን? (ዮሐ ፲፬፥፩-፪) ስለዚኽ ለማርያም ሞት ፈጽሞ ማልቀስ አይገባችኹም፤ ወደ እናንተ በፍጥነት ሳትመለስ በጭራሽ አልተዋትም፡፡ እኔም ራሴን ከእናንተ እንዳልሰወርኹት ኹሉ ድንግል እናቴም ፈጽሞ ራሷን ከእናንተ አትሰውርም፡፡ ስለዚኽ ኹልጊዜም ወደ እናንተ ስመጣ ድንግል እናቴን ከእኔ ጋር አብራ እንድትመጣ በማድረግ ነፍሳችኊ እንዲቀደስ አደርጋለኊ” አለ፡፡ እዚኽ ላይ አባቴ ጴጥሮስ እና የተቀሩት ደቀ መዛሙርት ለመድኀኒታችን “አምላካችን እና ጌታችን ከነጭራሹ ፈጽሞ የሞትን ጽዋ እንዳትጋፈጥ ማድረግስ አይቻልም ነበርን?” አሉት፤ መድኀኒታችንም “የእኔ ቅዱሳን ሐዋርያቶች ሆይ ይኼ ንግግር ከእናንተ በመምጣቱ በጣም ድንቅ ነው አላቸው፡፡ በመዠመሪያ የተናገርኹት ቃል ሊታበል ይችላልን? አይችልም አባቴ ከልክሏልና፡፡ ገና ከመዠመሪያውም ኹሉም ሥጋ የለበሰ ሰው ኹሉ ሞትን ማጣጣም ያስፈልጋቸዋል ብዬ ፍርድ ፈርጃለኊ (ዘፍ ፫፥፲፱)፡፡ እኔም የሰዎች ኹሉ ጌታ የኾንኹት በለበስኹት ሥጋ የተነሣ ሞትን ቀምሼ የሞትን ሰቈቃ ያጠፋኊት” አለ (ሮሜ ፭፥፲፯)፡፡ አባቴ ጴጥሮስም በዚኽ ጊዜ ላይ እንደገና “ከአንተ ጋር እንድነጋገር ፍቀድልኝ” አለው፡፡ ጌታም “ተነጋገር” አለው፡፡ አባቴ ጴጥሮስም “ጌታዬ ለእኛ በማዘን እመቤታችን የምቾታችን (የሐሤታችን) ምንጭ በመኾኗ ለጥቂት ጊዜ በሕይወት እንድትቆይ አድርግልን” አለው፡፡ መድኀኒታችንም ሲመልስለት እያንዳንዱ ሰው በዚኽች ምድር ላይ የተቀመጠለት የቆይታ ጊዜ አለ፤ ጊዜው ሲደርስም ለአንዲት ሰዓትም እንኳን በተጨማሪ ለመቆየት አይቻለውም አለው፡፡ አኹን ስለዚኽ ለእናቴ የተቀመጠላት ጊዜ ዛሬ ይፈጸማል፡፡ አኹን ሰውነቷን አኑራ እና ከእኔ ጋር በክብር ወደ ሰማያት መኼድ ይገባታልና፤ የሰማያትን ሥርዓት ተመልከቱ፣ አባቴ የውድ ልጁ መቅደስን፤ እኔን ጨምሮ እየጠበቅናት ነውና፡፡ ወደ አባቴ ሳልወስዳት በፊት እራሴ እኔ በቅዱስ መሥዋዕት ከርሷ ጋር እንባርካችኋለንና” አለን)፡፡
፱. “The women therefore that went with her, even the virgins that followed her, turned their face away, and all wept bitterly…” (ከርሷ ጋር በአንድነት ይኼዱ የነበሩትም ሴቶች ተከትለዋት የነበሩትም ደናግል ፊታቸውን አዙረው ኹሉም አምርረው በሲቃ ድምፅ አለቀሱ፤ ቅድስት ድንግል ማርያምም አብራቸው አለቀሰች፡፡ ቸሩ መድኀኒታችንም “ማርያም ድንግል እናቴ ሆይ ስለምን ታለቅሺያለሽ? አላት፤ አኹን ልቅሶሽን በመተው ለዘላለም ነዋሪ ወደኾነው ደስታ መኼድ አለብሽ አላት፤ ሐዘን እና ለቅሶሽን በመተው በሐሤት እና በደስታ ለዘላለሙ መኖር ይገባሻል፤ የምድር ነገሮች በሙሉ ትተሽ የሰማያት የኾኑትን መውረስ ይገባሻልና”፤ ድንግል ማርያምም ለመድኀኒታችን ስትመልስለት “ጌታዬ፣ አምላኬ እና ልጄ እንዴት ዐላዝን እና በልቤስ አላለቅስ? በጣም ብዙ ጊዜያት በሰው ልጆች ሞት በጣም ብዙ ቅርፆች እናዳሉት፣ ሊወስዳቸው ከመጣ በኋላም አስፈሪ እና አሰቃቂ ነገር እንዳለው ሲነገር ሰምቻለኊ፤ እነዚኽ ነገሮች ከኾኑ፣ እንዴት አላለቅስ እንዴት ብዬስ አስፈሪውን ቅርፁን ልመልከተው?” አለች፤ ጌታችን ኢየሱስም “ውዷ እናቴ ማርያም ሆይ ሞትን ፈጽሞ እንዳትፈሪው፣ ማንኛውንም የሞት ኀይል ለማውደም የሚችለው ከአንቺ ጋር አይደለምን? አላት፤ ብዙ ቅርጽ ያለው ጣዕረ ሞትን የዓለም ኹሉ ሕይወት እስትንፋስ የያዘው ከአንቺ ጋር እያለ እንዴት ትፈሪዋለሽን?” አላት፤ ጌታም በራሱ ራርቶ ራሱን ወደ ድንግል እናቱ አስጠግቶ እንባዎቿን ጠራርጎላት በመለኮታዊ ከናፍሮቹ ሳማት፡፡ ከዚያም ጌታ ኢየሱስ በመሠዊያዉ ላይ በመኾን ኹላችንንም ባረከን፣ የሰላም ሰላምታውን አቅርቦልን፣ አባቴን ጴጥሮስን “ፍጠን ወደ መሠዊያዉ ተመልከትና አባቴ ከሰማይ የላከልኝን ንጹሓት አልባሳትን አምጣልኝ ድንግል እናቴን ላልብሳት ምክንያቱም የርሷን ቅዱስ ሰውነት በምንም ዓይነት ከምድር የተገኘ ጨርቅ መሸፈን አይገባውምና” አለ፡፡ ከዚያም አባቴ ጴጥሮስ ያማረውን ውብ ሸማ፣ ንጹሕ፣ ቅዱስ፣ በጣም ውድ እና ጣፋጭ መዐዛ የሚረጨውን ይዞ መጣ፤ እጅግ ደማቅ ብርሃን የሚለቀውን ያማረ ሸማ ስንመለከት ኹላችንም በጣም ተደነቅን፡፡ መድኀኔ ዓለምም ያማረውን ሸማ ከአባቴ ጴጥሮስ ላይ ተቀብሎት በራሱ መንገድ ዕጥፋቶቹን በመዘረጋጋት፤ ድንግል እናቱን ጠርቷት፣ ተነሺ የእኔ ብራማ ርግብ ክንፎችሽ በወርቅ የተንቈጠቈጡት ወደ እኔ ነዪ አላት (መዝ ፰፯፥፲፫)፤ የእኔ ንጽሕት እና እንከን የለሽ ጠቦት ወደ እኔ ነዪ” አላት (መዝ ፷፰፥፴፩))፡፡
፲. “And she arose, the queen of all women, Mary the Virgin, the mother of the King of kings, to go unto her beloved Son, our Lord Jesus Christ…” (የሴቶች ኹሉ ንግሥት፣ ድንግል ማርያም፣ የነገሥታት ንጉሥ እናት ወደ ተወዳጁ ልጇ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ለመኼድ ተነሣች፡፡ ኹላችንም ከተቀመጥንበት ተነሥተን እጆቿን እና እግሮቿን እያነባን ሰላምታን ሰጠናቸው፤ ከዚያም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ውድ ልጇ ሰላምታ አቅርቦላት “ወደ ዘረጋኹልሽ አልባሳት ውስጥ ግቢ እና ፊትሽን ወደ ምሥራቅ መልሺ እና ጸሎት አቅርቢ፤ ከዚያ በኋላ መጐናጸፊያው ላይ ጋደም በይ እና በምድር ላይ ለተወለዱ ሰዎች በሙሉ ጸሎትሽን አሟይ” አለ፤ የሴቶች ኹሉ ልዕልት፣ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ የነገሥታት ኹሉ ንጉሥ እናት ከተቀመጠችበት ተነሥታ መድኀኒታችን በእጆቹ ወደ ዘረጋላት መሸፋፈኛ መኻከል ገባች፡፡ በቆመችበት ፊቷን ወደ ምሥራቅ አግጣጫ አዙራ በሰማይ ነዋሪዎች ቋንቋ ጸሎቷን አቀረበች፡፡ ጸሎቷንም እንደጨረሰች አሜን አለች፤ እኛም ኹላችንም ከተቀመጥንበት ተነሥተን አሜን ብለን መልስ ሰጠናት፡፡ ከዚኽ በኋላ በመሸፋፈኛ አልባሳቱ ላይ ጋደም ብላ እጆቿን ተደግፋ ወደ ምሥራቅ አግጣጫ ፊቷን አዞረች፡፡ ከዚያም መድኀኒታችን ከርሷ ጋር በቤተ መቅደስ ሲያገለግሉ ከነበሩትና መድኀኒታችንን እስከ እግረ መስቀል ሲከተሉ ከነበሩ ደናግል ጋር በአንድ ላይ እንድንጸልይ ለጸሎት እንድንቆም አደረገን፡፡ ክርስቶስ በተሰቀለበት ጊዜ ሴቶቹ ተከትለዋት መጥተው ነበር፡፡ እኛም በቤተ መቅደስ ለምን ማገልገል እንዳቆሙ ስንጠይቃቸው? እነርሱም የእግዚአብሔር አብ ቃል ክርስቶስ በተሰቀለበት ቀን ኹሉም ቦታዎች ሲለወጡ ተመልክተን ነበር አሉን፡፡ ፀሓይ ጨልማ ነበር፣ ጨረቃ ደም መስላ ነበር ከዋክብትም ከሰማያት ወደ ምድር ወድቀው ነበር፡፡ እኛም በጣም ፈርተን የቅዱሳን ኹሉ ቅዱስ ወደኾነው የጌታ ቤተ መቅደስ ውስጥ ሸሽተን ገባን በሩንም ጥርቅም አድርገን ዘጋነው፡፡ ወዲያውኑም ኀይለኛ መልአክ ከሰማይ በታላቅ ቁጣ በእጁ ውስት የሚያብለጨልጭ ሰይፍ ይዞ ወደ ምድር ሲወርድ ተመለከትን፣ በያዘው ሰይፍም መጋረጃውን መኻል ለመኻል ከላይ ወደታች እኩል በእኩል ቀደደው (ማቴ ፳፯፥፶፩)፡፡ ከዚያም ታላቅ ድምፅ “ኢየሩሳሌም ኢየሩሳሌም ሆይ ነቢያትን የምትገድል ወደ ርሷ የተላኩትንም የምትወግር ዶሮ ጫጩቶችዋን ከክንፎችዋ በታች እንደምትሰበስብ ልጆችሽን እሰበስብ ዘንድ ስንት ጊዜ ወደድኊ! አልወደዳችኹምም እነሆ ቤታችኊ የተፈታ ኾኖ ይቀርላችኋል” (ማቴ ፳፫፥፴፯) የሚል ሰማን እንደገና ስንመለከት ለመሠዊያው ተመድቦ የነበረው መልአክ በመሠዊያው በላይ ሰይፉን ይዞ በታላቅ ቁጣ ሲበርር ተመለከትን፤ እነዚኽ ነገሮች በሙሉ ሲኾኑ ባየን ጊዜ፣ ጌታ በሰዎቹ በጣም እንደተቆጣና በርግማን ሥር እንዳንወድቅ በማሰብ ከእኛ ጋር ወደነበረችው እናቱም በፍጥነት እንደመጣን ዐወቅን፣ ይኽነንም መጋረጃውን ከቀደደው የጌታ መልአክ አፍ ሰማን” አሉ (ማቴ ፳፯፥፶፩)፡፡ ፲፩. “The twelve virgin s therefore and all the women also who were with us, were all weeping with us together, …” (ዐሥራ ኹለቱ ደናግል እና ከእኛ ጋር የነበሩት ሴቶች በሙሉ ድንግል ማርያምን በዙርያዋ ከብበን የተማርነውን የሰማያዊ ምስጋና መዝሙር ስንዘምር ቆመን ስናለቅስ ነበር፡፡ ክርስቶስም ለእናቱ ክብር እጆቹን በጉንጮቿ ላይ አድርጎ ከጐኗ ተቀምጦ ነበር፡፡ ለረዥም ጊዜ በዝማሬ ላይ ሳለን ክርስቶስ ለእናቱ ሰላምታ አቅርቦላት ወደ ውጭ ይዞን ወጣ፡፡ ድንግልም “ኢየሱስ ሆይ እውነተኛው ያለምንም ነውር ነቀፋ የወለድኹኽ ልጄ፣ የኀያሉ እግዚአብሔር ልጅ እና ውዱ ልጄ ልለምንኽ፣ የወለድኻትን እናትኽን እንዳትረሳት፣ ጌታዬ ሆይ፣ የሞት ጥላ እንዳይቀርበኝ፤ ውዱ ልጄ ሆይ የአምባገነኑ የሞት ኀይሎች እና የድቅድቁ ጨለማ ሥልጣናት ይርቁ ዘንድ፡፡ የብርሃን መላእክት ይቅረቡኝ እንጂ ሞትን የማያውቁት ትሎች እንዳሉ ባሉበት ይኹኑ፡፡ የውጭው ጨለማ ብርሃን ይኹን፡፡ የሐሰት ከሳሾች አፍ ይዘጋ፡፡ በጥልቁ እንጦርጦስ የሚገኘው እሳት የሚተፋው ዘንዶ ወደ አንተ ስመጣ ሲመለከት አፉ የተዘጋ ይኹን፡፡ ውዱ ልጄ ሆይ የጥልቁ እንጦርጦስ አዛዦች ከእኔ እንዲሸሹ እና ነፍሴን እንዳያስፈራሯት እዘዛቸው፡፡ በእነዚኽ መንገዶች የሚገኙት አደናቃፊ ድንጋዮች ከፊቴ ይውደሙ፡፡ በመጥፎ ዐይኖቻቸው የሚያዩኝን በቀለኞችን ከልለኝ፡፡ ልክ እንደ ባሕር ማዕበል የሚናወጠው የሚንቀለቀለው የእሳት ወንዝ፣ ጻድቃን እና ኀጥኣንን ለኹለት የሚከፍለው በማልፍበት ጊዜ ነፍሴን ፈጽሞ እንዳይነካት፤ ምንም ኀፍረት በሌለበት ፊቴ አመልክኻለኹና ከዘመናት እስከ ዘመናት ኀይል እና ክብር የአንተ ናቸው” አሜን)፡፡
፲፪. “And our Lord Jesus Christ said to His mother with His gentle voice, Be of good cheer, O Mary my mother…” (ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱን ድንግል ማርያም ለስለስ ረጋ ባለ አስደሳች አንደበቱ ማርያም እናቴ ሆይ እጅግ ደስ ይበልሽ አላት፡፡ እነዚኽ ኹሉ ነገሮች በአንቺ ውስጥ ፈጽሞ ቦታ ስለሌላቸው ከአንቺ አርቄ አባርርልሻለኊ፤ በእነርሱ ፈንታ ለዘላለሙ ማረፊያሽ የኾኑትን የሰማያዊ ማረፊያ ቦታዎች እና በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም የሚገኙትን መልካሞች ነገሮችን አዘጋጅቼልሻለኊ፡፡ አካልሽ በውስጡ የሚሸፋፈንበት ከገነት የመጣውን ሰማያዊ መሸፈኛ እና እጅግ ያበቡትን የዘንባባ ዝንጣፊዎች አዘጋጅቼልሻለኊ፡፡ ቅዱስ ነፍስሽን ከእኔ ጋር ወደ ሰማይ በመውሰድ ለመልካሙ አባቴ በስጦታነት አበረክታታለኊ፣ እኔን የወለድሽኝ አንቺ ቅድስት ሆይ ከስጦታዎች ኹሉ እጅጉን ከፍ ያልሽ ስጦታ ነሽና” አላት፤ ጌታችን ሐዋርያቱን “እኔ የዓለም ሁሉ ሕይወት እስትንፋስ ባለኹበት ሞትን ማየት ስለማይገባት የውድ እናቴ ነፍስ መሰናበቻዋ ጊዜ በመቃረቡ ለጥቂት ጊዜያት ወደ ውጭ እንውጣ” አላቸው፡፡ እነሆ አኹን እኛን በመጠበቅ በአንድ ላይ ኹሉም የሰማያት ኀይሎች ኹሉ ተሰብስበዋልና፤ ስለዚኽ ርሷ ጋደም ብላ እንዳለች ትተናት ጌታን ተከትለን ኹላችንም ወደ ውጭ ወጣን፤ ከርሷ ጋር የተሰበሰቡት ደናግል ዮሐና እና ሰሎሜ እንዲኹም ኹሉም ታማኝ ሴቶች ሊያገለግሏት በውስጥ ቀሩ፡፡ ጌታችን በመግቢያው በር ላይ በውጭ በሚገኝ አንድ ድንጋይ ላይ ተቀምጦ ሳለ ኹላችንም ከብበነው በዙሪያው ቆምን፡፡ ወደ ሰማይ ተመልክቶ በከፍተኛ ድምፅ “ሞት ሆይ መኖሪያኽ በስተደቡብ በሚገኙት የማከማቻ ስፍራዎች የኾነው ድል ነሥቼኻለኊና ሥጋ በለበሱ ፍጡራን ላይም በሙሉ ሥልጣን ሰጥቼኻለኊ እና ወደ ድንግል እናቴ ና፣ ቅረባት ትመልከትኽ ግን ማርያም እናቴ ምንም ልታይኽ እስከማትችልበት ጊዜ ድረስ ማቃጠልኽ እና አሸናፊነትኽ ይውደም፡፡ ከዚያ በኋላ ግን (እናቴ ካረፈች በኋላ) ለዘላለሙ የምትለብሰውን አስፈሪ ቅርጽ እና ማቃጠልኽን እንዲኹም አሸናፊነት መልሰኽ ተጐናጸፍ፡፡ በአፍታ ቅጽበት እና በዐይን ብልጭታ ከሰው ልጆች ኹሉ ስሙ እጅግ አስፈሪ የኾነው ሞት ቀረበ፡፡ ልክ በዐይኖቿ እንዳየች ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይታ ልጇ ተቀምጦበት ወደነበረው ቦታ መጥታ በዕቅፉ ውስጥ ወደቀች፡፡ የእግዚአብሔር ቃልም በነበርንበት ቦታ ከመኻከላችን ተቀምጦ ሳለ ሰማይ እና ምድርን መላቸው፡፡ እንደ በረዶ ጸዐዳ የኾነውን የድንግል ማርያምን ነፍስ በዕቅፉ ውስጥ እንደያዘ ለነፍሷ የከበረ ሰላምታውን ሰጥቶ ባማረው ሸማ ጠቅልሏት ለሊቀ መልአኩ ለቅዱስ ሚካኤል በብርሃናማ ክንፎቹ እንዲሸከማት ሰጠው፣ ይኽም ለቅዱስ አካሏ ማኖሪያ ቦታ እስኪያዘጋጅ ድረስ ነበር፡፡ ኹሉም በዙሪያዋ ከበው የነበሩት ሴቶች ዕረፍቷን በተመለከቱ ጊዜ እጅግ ዐዝነው አለቀሱ፡፡ ሰሎሜም ወደ ውጭ ወጥታ በጌታዋ እግር ላይ ተደፍታ “ጌታዬ አምላኬ ተመልከት ውድ እናትኽ ዐርፋለች” ብላ አመለከችው፡፡ ዛሬ ታላቅ ዐዘን እና መነጠል የወደቀብን ለእኛ ወዮውልን፡፡ አንተ በአጠገቧ ብትኖር ኖሮ አትሞትም ነበር፡፡ ጌታ ኢየሱስም “እናቴ ድንግል ማርያም አትሞትም ይልቁንም ለዘላለም ትኖራለች፤ የእናቴ ሞት ሳይኾን የዘላለም ሕይወት ነው እንጂ” አለ፡፡ ቅዱሱ አመስጋኝ ዳዊትን በመንፈሳዊ በገናው ጮኾ በመዘመር “በጌታ ፊት የቅዱሳኑ ሞት እጅግ የከበረ ነው” (መዝ ፻፲፭፥፲፭) የነገሥታት ኹሉ ንጉሥ የኾነው የክርስቶስ እናት ማርያም ደስ ይበልሽ፤ ይኽ ስለ እውነተኛዋ ንግሥት ማርያም የተናገርኩት ትንቢት የተፈጸመበት ቀን ነው” (መዝ ፵፬፥፱) በማለት ዘመረ)፡፡ ፲፫. “And our Saviour arose from the stone, and went into the house,…” (መድኀኒታችንም ኹላችንም ከርሱ ጋር በአንድ ላይ እያለን ከተቀመጠበት ድንጋይ ተነሥቶ ወደ ቤት ውስጥ ገባ፡፡ የድንግል ፊት እንደ ፀሓይ እያበራ እና ሰውነቷ አስደሳች የሽቱ መዐዛን ሲረጭ አየን፡፡ በለቅሶ አኹን በእናቱ ድንግል ማርያም አካል ላይ አድርጎ “የእኔ እናት ማርያም ሆይ እግዚአብሔርን (እኔን) የሳምሽባቸው ከናፍሮችሽ የተባረኩ ናቸው፤ ወደ ምድር ሲመለከት መሠረቶቿ እንዲናጉና እንዲሸበሩ ለማድረግ የሚችለውን ከኀሊውን ልጅሽንና አምላክሽን (እኔን) ያየሽባቸው ዐይኖችሽ የተባረኩ ናቸው፤ ከሰማያት ነዋሪዎች ጋር በመላእክት ቋንቋዎች ስነጋገር የሰማሽባቸው ዦሮዎችሽ የተባረኩ ናቸው፤ አንቺ ሆይ በቃሉ ኀይል ምድርን የተሸከማትን የተሸከሙት የኖርኹባቸው ታናናሾች ክንዶችሽ የተባረኩ ናቸው፡፡ የእኔ ድንግል እናት ማርያም ሆይ ፍጥረትን ኹሉ የምመግበውን የመገቡት እና ያጠቡት ጡቶችሽ የተባረኩ ናቸው፡፡ በኀያሉ ዙፋን ላይ በክብር የምቀመጠውን እኔን በፍቅር ያስቀመጡኝ ጉልበቶችሽ የተባረኩ ናቸው፡፡ ለዘጠኝ ወራት የተሸከሙኝ ማሕፀኖችሽም የተባረኩ ናቸው፡፡ በመለኮታዊነቴ ብርሃን ብሩሃት የኾኑት ሥጋሽና ነፍስሽ የተባረኩ ናቸው” አላት)፡፡
፲፬. “Now when out good Saviour had said these things…’’ (አኹን ቸሩ መድኀኔ ዓለም ስለ እናቱ እነዚኽን ነገሮች ሲል እያነባ ነበር እኛም ኹላችንም ስናለቅስ ነበር፡፡ ከተቀመጠበት ተነሥቶ ሰማያዊ አልባሳቶቹን በማንሣት ቅዱስ አካሏን ሸፈነው፤ ርሱ፣ ጴጥሮስ እና ዮሐንስ፣ አልባሳቶቹን ከአካሏ ጋር በደንብ ታስረው ነበር፡፡ መድኀኒታችንም ለሐዋርያቱ “ተነሡ ለእኔ ቅዱስ ቤተ መቅደስ የኾነውን የእኔ ውድ እናት ቅዱስ አካሏን ወደ ላይ አንሥታችኊ እና የኀያሉ አልባሳት የተጠቀለሉበት እና የሰማያዊ ቦታዎች ዘንባባ ዝንጣፊዎች ያረፉበትን በዠርባችኊ ተሸከሙት” ብሎ ተናገራቸው፡፡ “በእኔ የተመረጥኽ ጴጥሮስ ሆይ ራሷን በትከሻኽ ተሸከም፣ ዮሐንስም እግሮቿን ተሸከም፤ እናንተ ወንድሞቼ እና ቅዱሳን አባላቶቼ (ኅዋሶቼ) ናችኹና፤ የተቀራችኹት ሐዋርያቶቼ በፊቷ ዘምሩላት፤ ኹላችሁም ከትንሽ እስከ ትልቅ ሳትሉ ወደ ምሥራቃዊቷ ኢየሩሳሌም ኢዮሳፍጥ ዐብራችኋት ኺዱ በዚያም እንደደረሳችኊ ከዚኽ በፊት ማንም ሰው ያላረፈበት ዐዲስ መቃብር ታገኛላችኊ፡፡ ቅዱስ አካሏን በዚያ ውስጥ ያርፍ ዘንድ አለውና ለሦስት ቀናት ተኩል ትጠብቁታላችኹና፡ ፈጽሞ እንዳትፈሩ እኔም ከእናንተው ጋር ነኝና” አለ፤ አኹን መድኀኒታችን የቡራኬ ንግግሩን አድርጎ እንደጨረሰ ዘማሪው ቅዱስ ዳዊት “ሃሌ ሃሌ ሉያ በኋላዋ ደናግሉን ለንጉሥ ይወስዳሉ ባልንጀሮችዋንም ወደ አንተ ያቀርባሉ” በማለት ዘመረ (መዝ ፵፬፥፲፬)፡፡ ከዚኽ በኋላ ጌታ ኢየሱስ የሰላም ሰላምታውን ሰጠን ኹላችንም አመለክነው፡፡ እንደገናም ዳዊት “ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ አቤቱ ወደ ዕረፍትኽ ተነሥ አንተና የመቅደስኽ ታቦት ይኽቺውም ነውር ነቀፋ የሌለባት ንጽሕት ማርያም ናት” (መዝ ፻፴፩፥፰) በማለት አመሰገነ)፡፡
፲፭. “Straightway our Saviour rode upon His chariot of Cherubim,…” (በቀጥታ መድኀኒታችን በኪሩቤል ሠረገላ ላይ ኾኖ፣ ኹሉም የሰማያት ሥልጣናት በዝማሬያቸው ተከትለውት ሳለ አየሩ በጣፋጭ መዐዛ ተትረፍርፎ ነበር፡፡ የእናቱን ነፍስ በዕቅፉ ተቀብሎ፣ ባማረ መጐናጸፊያ ጠቅልሎት፣ የብርሃን ብልጭልጭታን በመላክ ኹላችንም እየተመለከትነው ወደ ሰማያት ኼደ፡፡ ከዚያም ወዲያውኑ የድንግልን አካል ወደ ላይ በማንሣት አባቴ ጴጥሮስ ራሷን፣ ዮሐንስ እግሮቿን ተሸክመው ሳለ የተቀሩት ሐዋርያት በእጆቻቸው የዕጣን ማዕጠንት ይዘው በአንድ ላይ ከእኛ ጋር እየዘመሩ ኹሉም ደናግል ከኋላችን ተከትለውን በምሥራቃዊቷ ኢየሩሳሌም ኢዮሳፍጥ መስክ ተብላ ወደምትታወቀው ኼድን፡፡ ርጉማን የአይሁድ ሕዝቦች ጌታችንን ዐምፀው ወደ ገደሉባት ስንደርስ ቅዱሳን አባቶቻችን ሐዋርያት በታላቅ ድምፅ ሲጸልዩ ድምፅ ሰሙ፤ ከዚያም ርስ በርሳቸው “በዚኽ ከተማ ዛሬ በቀን የሞተው ማን ነው” ተባባሉ፡፡ አንዳንዶቹም “እኛ በመስቀል ላይ የሰቀልነው የናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ እናት ናት እነሆ ወደ መቃብሩ እየወሰዷት ነው” ብለው መለሱ፡፡ ከዚያም ርስ በርሳቸው ተመካክረው ሰይጣን ልባቸውን አደንድኖት በሰይጣናዊ ዕብሪት ተነሣስተው እኛን ገድለው የድንግል ማርያምን አካል ለማቃጠል ዐስበው ወደ እኛ መጡ፤ ይኽነንም ከዚያ በኋላ ለእኛ እንደተናዘዙልን፡፡ ወደ እኛ እየቀረቡ ሲመጡ እነሆ እኛንም እነርሱንም የእሳት ግድግዳ ከበባቸው ዐይኖቻቸውም በድቅድቅ ጨለማ ተዋጠ፡፡ ጌታም ከዚኽ በፊት ልክ በግብጻውያን ላይ አድርጎት እንደነበረው ማንም ሊሰማው በሚችል ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ዋጣቸው (ዘፀ ፲፥፳፪-፳፫)፡፡ ግን የድንግል ማርያምን አካል ሐዋርያቱ እንደተሸከሙት በመድኀኒታችን ቃል መሠረት በመቃብር ውስጥ አስቀመጡት እና ጥበቃ ለማድረግ ሦስት ቀን ከተኩል በዚያው ቆዩ)፡፡
፲፮. “Now the Jews, when they saw the great anger which…” (አይሁድ አኹን ከጌታ የወረደባቸውን ታላቅ ቁጣ ሲመለከቱ ጮኸው በማልቀስ እንዲኽ በማለት ተማጸኑ፣ “የኢየሱስ ክርስቶስ እናት ማርያም ሆይ ርጂን፡፡ ከአንቺ የተወለደው ኢየሱስ ክርስቶስ በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነው፡፡ እኅታችን ማርያም ሆይ ከዘር ሀረጋችን ትመዘዥያለሽና እና ምሕረትን ለምኝልን፡፡ ለአፍታም እንኳን ምንም ጥፋት አጥፍቶ በጭራሽ የማያውቀውን ክርስቶስ ልጅሽን በድለናል፡፡ ስለዚኽ እኅታችን ማርያም ሆይ ምሕረትን አውርጅልን እና የዐይኖቻችንን ብርሃን ለግሺን” አሉ፡፡ ወዲያውኑም ዐይኖቻቸው ተከፍተው ብርሃን አዩ፤ ቢፈልጉም የድንግልን ቅዱስ አካል አላገኙትም (ወደ ገነት ከዮሐንስ ጋር በመነጠቁ)፡፡ በኾነው ድንቅ ተአምር እጅግ ተደምመው ድምፃቸውን ከፍ በማድረግ ጮኸው “አንድዬ ልጁን ወደ ዓለም የላከው ርሱ የእስራኤል አምላክ ነው፤ በእውነት ታላቅ ኀጢአት በመፈጸም ጥፋተኞች ነን” አሉ)፡፡
፲፯. “Now when they had reached mid-day on the fourth day, the apostles being gathered together with one another…” (በአራተኛው ቀን እኩለ ቀን እየተቃረበ ሲመጣ ሐዋርያቱ አንዳቸው ለአንዳቸው ከደናግል ጋር የድንግልን ሥጋ ሊያኖሩበት በነበረው በመቃብሩ ስፍራ በመሰብሰብ ለድንግል ማርያም ክብር ዝማሬ እና የምስጋና ዜማ አቀረቡ፤ እነሆ ልክ እንደ መለከት ያለ ድምፅ በከፍተኛ ኹኔታ ከሰማይ መጣ “እስከ ሰባተኛው ወር ድረስ ወደቦታው ኹላችኹም መኼድ ይኖርባችኋል፡፡ እነሆ የካህናት አለቆችን እና የኹሉንም አይሁዶች ይኽነን ቦታ ከዚኽ በኋላ እንዳያዩት ወይም እንዳያውቁት ወይም አካሏን ከእኔ ጋር ወደ ሰማይ እስክወስደው ድረስ የድንግልን አካል ለማግኘት እንደይፈልጉ ልባቸውን አደንድኜዋለኊ፡፡ ከእናንተ ጋር የነበሩት ደቀ መዛሙርቶች እና ደናግል በሙሉ በዐሥራ ስድስተኛው ወር ሚዞሪ (ነሐሴ ፲፮) እናቴን ድንግል ማርያምን ነፍሷን ወደ ሥጋዋ መልሼላት ልክ በምድር ከእናንተ ጋር ትኖር እንደነበረው ከእኔ ጋር ወደ ሰማይ ስወስዳት እንድትመለከቱ ትንሣኤ ለኹሉም ሥጋ መኾኑን ኹላችኹም በልባችኊ እንድታምኑ ዘንድ ትመጣላችኊ”፤ ይኽነን ድምፅ እንደሰማን እግዚአብሔርን እያመሰግን ነበር፤ ከተቀመጥንበት ተነሥተን ጸለይን፣ ወደምንኖርበት ቤትም ተመለስን፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም በመለየታችን በታላቅ ዐዘን እና ልቅሶ ውስጥ ወደቅን እግዚአብሔር የልባችንን ዐዘን እንዲያቀልልን እና ርሷን ደግሞ እንዲያሳየን በየቀኑ ስንጸልይ ቆየን፡፡ እግዚአብሔርን የተሸከመች ቅድስት ድንግል ማርያም ነፍሷ ከሥጋዋ ከተለየችበት የሚዞሪ (ከጥር) ወር ዠምሮ ሰባተኛው ወር (ነሐሴ) ላይ ደረስን፣ በዚኽ በዐሥራ ዐምስተኛው ቀን ላይ የድንግል አካል ወደነበረበት መቃብር ስፍራ ተሰበሰብን፣ ደናግልም ከእኛ ጋር በአንድ ላይ ነበሩ፡፡ ሌሊቱን በሙሉ ስናይ እና ስንዘምር፣ የዕጣን መሥዋዕት ስናቀርብ፣ ደናግልም መብራት ሲያበሩ ዐደርን)፡፡
፲፰. “Now at the hour of the light on this same night, which is the morning of the sixteenth of the month Mesore,…” (በዐሥራ ስድተኛው ሚዞሪ (ነሐሴ) ጠዋት በተመሳሳይ ምሽት በብርሃን ሰዓት ላይ፣ በምንኖርበት ቦታ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ክብር ወደ እኛ መጣ፣ “ቅዱሳን ሐዋርያቶቼ ሰላም ለእናንተ ይኹን የአባቴ ሰላም ከእናንተ ጋር ይኹን” አለን፡፡ እኛም ተደፍተን አመለክነው፣ ርሱም ኹላችንንም ባረከን፣ እንዲኽም አለን፣ “በዚኽ ታላቅ ዐዘን፣ የልብ ስብራት እና ጥልቅ ለቅሶ ውስጥ ናችኹን?”፤ አባቴ ጴጥሮስም “ጌታዬ እና አምላኬ እንዲኽ ጥልቅ ዐዘን ውስጥ የወደቅነው በእናትኽ ድንግል ማርያም እና በኹላችን እመቤት አካላዊ ሞት የተነሣ እና ከሞተችበት ጊዜ ዠምሮ ቃል እንደገባኽልን ደግመኽ ስላላሳየኸን ነው” አለው፡፡ ጌታም “የውድ እናቴ አካል እነሆ፣ በአባቴ ትእዛዝ መሠረት በመላእክቶቼ እና በእናንተ ይጠበቃልና ምክንያቱም የልጁ የእኔ ቤተ መቅደስ ነውና፤ ሰውነቷ ግን በሰማይ ሰማያዊ ቦታዎች ላይ በከፍተኛ ቦታዎች ላይ በሚገኙ መላእክት ዝማሬ ታጅቧል፡፡ እዚኽ ላይ በተውኹላችኊ ነገሮች ፈንታ በገባኹላችኊ ቃል ኪዳን የአኗኗሯን ክብር ለመግለጽ ወደዚኽ ወዳላችኹበት እንድትመጣ ልኬባታለኍ”፡፡ መድኀኒታችን ከእኛ ጋር በመነጋገር ላይ ሳለም ከፍ ባለ ቦታ ላይ የምስጋና መዝሙር ሰማን፡፡ ወዲያው ስንመለከት አንድ ትልቅ የእሳት ሠረገላ ተመለከትን፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምም በላዩ ላይ ተቀምጣበት በኪሩቤል መንኰራኲር እየተሳበና ከፀሓይ እና ከጨረቃ ዐሥር ሺሕ እጥፍ እያበራች መጥታ በመኻከላችን ቆመች (መሓ ፮፥፲፤ ራእ ፲፪፥፩)፡፡ እኛም በከባድ ፍርሃት ወድቀን በፊታችን ተደፍተን አመሰገንናት፤ ርሷም እጆዎችዋን ወደ እኛ ዘርግታ ኹላችንንም በመባረክ የሰላም ሰላምታዋን አቀረበች፡፡ እንደገናም በታላቅ ደስታ እና መቀደስ ውስጥ ኾነን አመሰገንናት፤ እዚኽ ላይ እምነት የለሽ በኾኑት የሰው ልጆች የተነሣ የማንናገራቸው ታላቅ እና ድብቅ ምስጢራትንም ነገረችን፡፡ (ዳግመኛ ለማሳየት) ጌታም ወደ መቃብሩ በመጣራት የድንግል እናቱን አካል በማስነሣት ነፍሷንም እንደገና ወደ ሥጋዋ በማስገባት ልክ ቀድሞ በሥጋ እንደምናውቃት በሕይወት አየናት፡፡ መድኀኒታችንም እጆቹን ዘርግቶ ከርሱ ጋር በሠረገላው ላይ አስቀመጣት መድኀኒታችን ለስለስ ባለ ድምፅ “እነኋት ውድ እናቴን” አለን፡፡ በዚኽች ምድር ለ፱ ወራት በማሕፀኗ የተሸከመችኝ እና ከማር የሚጣፍጡትን ጡቶቿን ለ፫ ዓመታት ያጠባችኝ ርሷ ነበረች አለን፤ እነኋት ፊት ለፊትም እይዋት፣ በእኔ አማካይነት ከሞት ተነሥታ ኹላችኹንም ባርካችኋለች አላቸው፡፡ አኹን ስለዚኽም ተጋድሏችኹን እስክታጠናቅቁ ድረስ ፈጽሞ ከእናንተ አልለይም፡፡ አኹንም ተነሡ ወደ መላው ዓለም ኼዳችኊ በየደረሳችኹበት ኹሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሰዎችን አጥምቁ ኹሉንም ያስተማርኋችኹን ነገሮች እንዲያከብሩ አስተምሯቸው” አለን (ማቴ ፳፰፥፲፱)፤ መድኀኒታችን እነዚኽን ነገሮች እየነገረን ቀኑን ሙሉ ከእናቱ ድንግል ማርያም ጋር ከእኛ እና ጋር ዐሳልፏል፡፡ ከዚያ በኋላ የሰላም ሰላምታውን ሰጥቶን መላእክት በፊቱ እየዘመሩለት በክብር ወደ ሰማያት ዐረገ)፡፡
፲፱. “This is [the end of] the life of the Lady of us all, the holy God-bearer Mary, on the twenty-first of Tobi and her assumption on the sixteenth of Mesore….” (ይኽ የኹላችንም እመቤት አምላካችንን የተሸከመች ቅድስት ድንግል ማርያም ዕረፍተ ሥጋዋ በኻያ አንደኛው የጦቢ ወር (ጥር ፳፩) ሲኾን በዐሥራ ስድስተኛው የሜዞሪ ወር (ነሐሴ ፲፮) በሥጋ ተነሥታ ዐርጋለች፡፡ እኔ ኢቮዲየስ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የአባቴ ጴጥሮስ ደቀ መዝሙር በዚኽ ጽሑፍ ውስጥ ከተነገሩት ሐዋርያት ጋር በአንድ ላይ በመኼድ፤ እነዚኽ ኹሉ ነገሮች ሲኾኑ ተመልክቼያለኊ፡፡ እነዚኽን ክስተቶች የሚነግራችኊ ሌላ ሰው ሳይኾን እኔው ራሴ ነኝ፤ ግን እነዚኽን ነገሮች በራሴው ዐይኖች ያየኋቸው እንዲኹም በዦሮዎቼ የሰማኋቸው ናቸው፤ እነዚኽ ክስተቶች ያልረከሰችው ነውር ነቀፋ ፈጽሞ የሌላት የአምላካችን የክርስቶስ እናት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ዕረፍት የነገርኋችኍ ናቸው፡፡ ትክክለኛው ዳኛ በሕያዋን እና በሙታን ላይ የሚፈርደው እግዚአብሔር በእነዚኽ ቃላት ላይ ምንም እንዳልቀነስኊ ወይም እንዳልጨመርኊ ምስክሬ ነው፡፡ የኹላችን እመቤት ቅድስቲቱ የእግዚአብሔር እናት ማርያም ክብረ በዓሏን እስከዛሬም ድረስ የምናከብርላት በእውነት የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጁ የእኛ አምላክ ከኾነው ከተወደደው ልጇ ከኢየሱስ ክርስቶስ ታማልደን፤ ለተቸገሩ ድኾች ሰዎች አምላክን በወለደች በቅድስት ድንግል ማርያም ስም ምፅዋትን እንስጥ፣ በባዕድ ሀገር እንዳንሰቃይ ታማልደን፣ ጌታችን እና አምላካችን እግዚአብሔር ምሕረት እንዲሰጠን እና ይቅር እንዲለን ታማልደን፤ አርምሞ ጽርዐት በሌለው ጸሎት በመዓልትም በሌሊትም ጮኽ ብለን ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ይቅርታኽን በእኛ ላይ አኑር ከባሕርይ አባትኽ ከአብ ከአንተ ጋር በተካከለ ሕይወትን በሚሰጥ ከባሕርይ ሕይወትኽ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር ጽንዕ ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን እያልን እንዘምር)፡፡ ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ ሙሉውን “ነገረ ማርያም በሊቃውንት ክፍል አንድ” ከሚለው መጽሐፌ አንብቡ የእመቤታችን በረከት አብዝቶ ይደርብን


Friday, March 6, 2015

ደብረ ዘይት

በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ

የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድ ነው?/ማቴ. 24፣3/

በዓቢይ ጾም ውስጥ ካሉት ሳምንታት ደብረ ዘይት 5ኛው ሳምንት ላይ ይውላል፡፡ ደብረ ዘይት ትርጉሙ የወይራ ዛፍ ተራራ ማለት ሲሆን፣ ይህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኢየሩሳሌም በሚገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ቅዱሳን ሐዋርያት” የዓለሙ ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድነው?”/ማቴ. 24፣3/ ብለው ጠይቀውት እርሱም የማይቀረውን የዓለም ፍጻሜና አስቀድመው የሚፈጸሙ ምልክቶችን አስረድቷቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ በደብረ ዘይት ሳምንት ታስበዋለች፤ ለምእመናኑም ከዘመኑ ሁኔታ አንጻር በመጻሕፍት የተጠቀሱትን የትንቢት ምልክቶቹን ከተግባራዊ የዓለም ክንዋኔዎች አንጻር በማገናዘብ ታስተምራለች፡፡ በመሆኑም በቤተ ክርስቲያናችን በደብረ ዘይት ሳምንት ምጽአትን አስመልክቶ የሚነገሩ ምስጢራት እጅግ ሰፊ ናቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ጽሑፍ በመጠኑ የምናየው ከቅዱሳት መጻሕፍት አንጻር በዓለም እየተከሰቱ ካሉ ወቅታዊ ምልክቶች ጋር በማገናዘብ ይሆናል፡፡

የሰው ልጅ ከሥነ ፍጥረት መነሻ ጀምሮ ስለ ራሱ መጨረሻና ስለ ዓለም ፍጻሜ ምንነት ማወቅን እንደሚሻ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ከነዚህም በተለይ ቤተ ክርስቲያን በደብረ ዘይት እለት የምታስተምረው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት’ የዓለሙ ፍሳሜስ ምልክቱ ምንድነው?/ማቴ. 24፥3/’ በማለት የጠየቁት ጥያቄ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ከመለሰላቸው ዋናውና ቀዳሚው የምጽአቱ ምልክት የሐሳዊ መሲህ መምጣት ነው፡፡ ሐሳዊ መሲሕ ማለት በቀጥታ ትርጉሙ ሐሰተኛ የሆነ በስሙ ማለትም በኢየሱስ፣ በክርስቶስ፣ በአምላክ ስም የሚመጣ የክርስቶስ ተቃዋሚ ማለት ነው፡፡ ትርጉሙን አስፍተን ስናየው፣ ደግሞ ከሃይማኖት ጋር ተያያዥ የሆኑና ያልሆኑ በዓለም እየተካሄዱ ያሉ ሐሰተኛ ጉዳዮችንና የጥፋት መንገዶችን ያጠቃልላል፡፡ የሐሳዊ መሲሕ የጥፋት ሥራዎች ሳያውቁም ሆነ በተለይ ሆን ብለው በዓለማውያንና በክፉ መናፍስት ተከታዮች እየተፈለሰፉ በሚከሰቱ ሁኔታዎች የሚካሄዱ ናቸው፡፡ ከእግዚአብሔር የተገኙ የሃይማኖት የሥነ ተፈጥሮ የጋብቻና የመሳሰሉ ድንበሮች ማፍለስን ዓላማ ያደረጉ፤ እንዲሁም መንፈሳዊ ባህል፣ ሰብአዊ ክብርና የእድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ ሁሉ ከሐሳዊ መሲሕ መደብና ከዓለም ፍጻሜ ምልክትአንጻር የሚታዩ ናቸው፡፡ በዝርዝር ለማየት የሚከተሉትን ነጥቦች እንመልከት፣

1. የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ፡- ”አባቶችህ ያኖሩትን /የሠሩትን/ የቀድሞውን የድንበር ምልክት አትፍልስ” ምሳ.22፥28፣ 23፥10 አፈጻጸሙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት እንዳያውቁ ከማድረግ ይጀምራል፡፡ከዚህም አንዱ ሐሳዊ መሲሕ በእግዚአብሔር ስም በተለያየ ሁኔታና መንገድ መገለጥ ነው፡፡ ”እስመ ብዙሃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ፤ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ብዙ ሰዎች በኔ ስም ይነሣሉና” /ማቴ. 24፣5/፡፡ ይህም እንደ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና የቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት መሠረት፣ ከክርስቶስ ወደ ሰማይ ማረግ በኋላ የሚመጣ፣ ክርስቶስን የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ ነው ብሎ የማይሰብክ ሁሉ፤ ሌላ አምላክን የሚሰብክ ሁሉ መደቡ ከሐሳዊ መሲሕ ትምህርት ይመደባል፡፡ በመሆኑም ከዚህ በፊት ያለፉ፣ አምላክ ነን ብለው የተነሡ እንደ ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ /ሐዋ. ሥራ. 5፣36-37/ የመሰሉ ሁሉ ከዚያም በኋላ በየጊዜው የተነሡና በዚህም ወቅት የዋሁን ሕዝብ ”ኢየሱስ ነኝ፣ ኢየሱስ በኛ ዘንድ አለ” እያሉ የሚያጭበረብሩ ሁሉ ሐሳውያነ መሲሖች ናቸው፡፡ ከዚህም ሌላ ክርስቶስን ከአብ የሚያሳንሱ፣ ”ሎቱ ስብሐት” ነቢይ ነው ብለው የሚያምኑ፣ በመናፍስት አሠራር የሚጠነቁሉ፣ በማቴሪያሊስት /ቁሳውያን/ ወይም በኢቮሉሽን /በዝግመተ ለውጥ/ ትምህርት አምነው አምላክ የለም የሚሉ ሁሉ፣ ወዘተ የሐሳዊው መሲሕ አካላት ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ ”ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማይታመን መንፈስ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም የክርስቶስ ተቃዋሚው መንፈስ ነው፤ ይህም እንደማመጣ ሰምታችኋል፥ አሁንም እንኳ በዓለም አለ።” /1ዮሐ. 4፣3/ በማለት ይመሰክርባቸዋል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አሁንም በመልእክቱ ”ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፤ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን።” /1ዮሐ. 2፥18/ ይለናል፡፡ ከዚህ የምንረዳው የክርስቶስ ተቃዋሚ መምጣት የምጽአት ጊዜው መቃረብ ምልክት መሆኑን የማያሻማ ሀሳብ ያደርገዋል፡፡ በተጨማሪም የምጽአትን መቅረብ የሚያመለክቱ፣ ስለ ሐሳዊው መሲሕ እና ከርሱ ጋር ተያያዥ ስለሆኑ ወቅታዊ ጉዳዮች ተዛማጅ የሆኑትን የሚከተሉትን ትንቢቶች እንመልከት፣

ሀ. ”የአውሬው ምስል ሊናገር እንኳ ለአውሬውም ምስል የማይሰግዱለትን ሁሉ ሊያስገድላቸው፥ ለአውሬው ምስል ትንፋሽ እንዲሰጠው ተሰጠው። ታናናሾችና ታላላቆችም ባለ ጠጋዎችና ድሆችም ጌታዎችና ባሪያዎችም ሁሉ በቀኝ እጃቸው ወይም በግምባራቸው ምልክትን እንዲቀበሉ፥ የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር ያለው ምልክት የሌለበት ማንም ሊገዛ ወይም ሊሸጥ እንዳይችል ያደርጋል። ጥበብ በዚህ አለ። አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፥ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው።” /ራእ. ዮሐ. 13፥16-18/ የሚለው የቅዱስ ዮሐንስ ራእይን ሊፈታ ከሚችልበት ትርጉም አንዲት ቅንጣት ብቻ ከዘመኑ አንጻር ብናይ ’የሚናገር የአውሬው ምስል’ ማለትም ለሱ ያልተገዙትን ወይም ቁጥሩን ያልያዙትን የሚናገርባቸው፤ ምልክቱን ያልተቀበሉትን ሊገዙና ሊሸጡ እንዳይችሉ ያደርግል ማለት መኖር፣ መሥራት፣ መሸጥ፣ መለወጥ ወዘተ የሚያግዳቸው ሲል አሁን ባለን ወቅታዊ የዚህ ዓለም አኗኗር አንጻር ሲታይ ተመሳሳይ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለምሳሌ፣ መታወቂያ ወረቀት፣ ፓስፖርት፣ ቪዛ፣ የመኖሪያ ፈቃድ ወዘተ በዓለም አጠቃላይ አሠራር እና ባንድ ሰው የመኖር ማንነት ሚና ላይ ተጽእኖ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መታወቂያ ወረቀቶች የሌሉት ሰው ካለበት የትም መንቀሳቀስ አይችልም፡፡ ከዚህም በላይ ጉዳዩን ስናሰፋው በሰለጠኑት ዓለማት አሠራር የእያንዳንዱ ሰው የጣት አሻራ ኮምፒውተራይዝድ በሆነ መንገድ የተደራጀ በመሆኑ፣ እዚያ አደረጃጀት ውስጥ ካልተካተተ በቀር እዚያ ሀገር ሊኖር፣ ሊዘዋወር፣ ሊሠራ፣ ሊነግድ ወዘተ አይችልም፡፡ ለምሳሌ፣ አንድ እዚህ የኮምፒውተር ድር አደረጃጀት ውስጥ ያለ ሰው የትም ዓለም ቢሄድ በጣቱ አሻራ ይታውቃል፡፡ በትንቢቱ” አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፥ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው።”  የሚለው ይህን የሚያደራጀው ጉዳዩን የሚያስተሳስረው ሌላ አካል ሳይሆን ሰው መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት የሚለው ቁጥር የሰው ልጅ የጅማት ቁጥር ነውና፡፡

ለ. ሌላው የምጽአት መቃረብ ምልክት የሐሳዊው መሲሕ ዘመቻን አውቀው በድፍረት፣ ላላወቁት በረቀቀ መንገድ እግዚአብሔርን ያመለኩ አስመስሎ የእግዚአብሔርን ስም፣ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ቅዱሳንን፣ ባጠቃላይ በሰማይ የሚያድሩትን መስደብ ነው፡፡ እነዚህም ተግባራት በተለያዩ ዘመናት ሲፈጸሙ የቆዩ ናቸው ዛሬም ተጠናክረው እየተፈጸሙ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ፣ ሩቅ ሳንሔድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችንን እየተፈታተነ ያለው የተሐድሶ ሤራ ዋናው ተቃውሞው የወልድን አምላክነት፣ የድንግል ማርያምን ክብርና አማላጅነት፣ የታቦትንና የመስቀልን ክብር፣ የቅዱሳንን ክብርና አማላጅነት ነው፡፡ በመሆኑም ተሐድሶ በሥራው የአውሬው መንፈስ አራማጅና መንገድ ጠራጊ መሆኑን ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ በማለት ያረጋግጥልናል፡፡ ”ለዘንዶውም ሰገዱለት፥ ለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፤ ለአውሬውም፡- አውሬውን ማን ይመስለዋል፥ እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል? እያሉ ሰገዱለት። ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፥ በአርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው። እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ። ቅዱሳንንም ይዋጋ ዘንድ ድልም ያደርጋቸው ዘንድ ተሰጠው፥ በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው። ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል።” /ራእ. ዮሐ. 13፣4.8/ እንዲል፡፡

ሐ. ሌላው በዓለም ላይ የሚታየው በሰዎች ዘንድ ክብር፣ ዝናና ታዋቂነትን ለማግኘት ሲባል ራስን ከፍ ማድረግና እንደ አማልክት መቁጠር ከሐሳዊው መሲሕ ያስመድባል፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንደገለጸው የሰናዖር ሰዎችን ኀጢአት ስናሰተውል የተነሡበት ዋናው ነጥብ ’ስማችንን እናስጠራ’ የሚለው ነበር፡፡” ኑ ለእኛ ከተማና ራሱ ወደ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ፤ በምድር ላይ ሳንበተንም ስማችንን እናስጠራው አሉ።” /ዘፍ. 11፥4/ ነው የሚለን፣ በዚህ እኩይ አሳብ ምክንያት እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ደባለቀባቸው፡፡ የሰናዖር ሰዎች ያሰቡትናየተመኙት ትውልዱ እግዚአብሔርን ማድነቅ ትቶ፣ ለዘለዓለም ስማቸውን ሲጠራቸው፣ ሲያደንቃቸው መኖርን ነበር፡፡ ዛሬም ብዙዎቹ ይህንን የሰናዖርን ኀጢአትና የጥፋት ጉዞ እንደ ዓላማ ይዘው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡
2. የሥነ ተፈጥሮ ሕግ ድንበር መጣስ አንዱ የጊዜው መቃረብ ምልክት ነው፡፡ እግዚአብሔር የፈጠረው ፍጥረት ፍጹም በመሆኑ፣ ይህ ቀረህ፣ ይህ ይጨመርልህ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት፣ ሰው ለተለያየ ጥቅም በሚል ሰበብ ዝርያቸው የተለያዩ የሆኑትን ፍጥረታት ማዳቀልንና ማደበላለቅን ተያይዞታል፡፡እንስሳትና ተክሎችን ለማባዛት የማያደርገው ጥረትና  የማዳቀል ዘዴ የለም፡፡ በተቃራኒውም የሰውን ቁጥር ለመቀነስ የማያደርገው ሩጫ የለም፡፡ በመሆኑም ውጤቱ የሰውን ቁጥር ለመቀነስ ሲባል በሚደረጉ ሕክምናዎች ሰዎች ለተለያዩ በሽታዎች ተዳርገዋል፡፡ በሚደረገውም ማበረታታት በሠለጠኑት ዓለም ብዙዎቹ የግብረ ሰዶም ፈጻሚና አስፈጻሚ ሆነዋል፡፡ ይህ አሠራር አምላክ የሠራውን የፍጥረት ሕግ በማጣጣል ሰው ላሻሽል ወደሚል ያዘነበለ በመሆኑ የሰውን ልጅ ቅጥ ያጣ ድፍረት ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ግን ሥነ ፍጥረቱን እንዲያደባልቁበት አይፈልግም፡፡እግዚአብሔር ለሊቀ ነቢያት ሙሴ ”ሥርዓቴን ጠብቁ። እንስሳህ ከሌላ ዓይነት ጋር አይደባለቅ፤ በእርሻህም ሁለት ዓይነት ዘር አትዝራ” /ዘሌ. 19፣ 19፤/ ማናቸውም ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ጸያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ፤ ደማቸው በላያቸው ነው።” /ዘሌ 20፣ 13/ በማለት ያሰተምረናል፡፡

3.    በጋብቻ ላይ የሚደረግ ርኩሰትን ስንመለከትም በየትኛውም ዓለም የፍርድ ቤቶች ትልቁ ሥራ ማፋታት ሆኗል፡፡ ምክንያቱም ተጋቢዎች ባንድ ላይ እንዳይኖሩ አውሬው /አስማንድዮስ/ የጋብቻ ጠላት በመሆን ስለነገሠ ፈተናውን መቋቋም አልቻሉምና ነው፡፡ ስለዚህ አስማንድዮስ ከዛ ይልቅ ግብረ ሰዶምን እያበረታታ በአንዳንድ ሀገሮች እንደሚታየው ወንድ ከወንድ፣ ሴት ከሴት ጋር እያቆራኘ በቤተ ክርስቲያኖቻቸው” ጋብቻ እስከ መፈጸም አድርሷቸዋል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፣” ስለዚህ እርስ በርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሔር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኵሰት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ይህም የእግዚአብሔርን እውነት በውሸት ስለ ለወጡ በፈጣሪም ፈንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፤ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን። ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፤ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባሕርያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፤ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስሕተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ። እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ዓመፃ ሁሉ፥ ግፍ፥ መመኘት፥ ክፋት ሞላባቸው፤ ቅናትን፥ ነፍስ መግደልን፥ ክርክርን፥ ተንኰልን፥ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፤ የሚያሾከሹኩ፥ ሐሜተኞች፥ አምላክን የሚጠሉ፥ የሚያንገላቱ፥ ትዕቢተኞች፥ ትምክህተኞች፥ ክፋትን የሚፈላለጉ፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያስተውሉ፥ ውል የሚያፈርሱ፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ምሕረት ያጡ ናቸው፤ እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም።” /ሮሜ.1፥24-ፍጻሜ

4.    መንፈሳዊ ባህል፣  የክህነት ክብር፣ ሰብአዊ ክብርና የእድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና  ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ፣ በሚለው ዙሪያ ስንመለከት በቀላሉ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ያለውን ማየት እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥ ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ እነዚህ ደግሞ ራቅ። ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ፥ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ሁል ጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ፥ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና። ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደተቃወሙት፥ እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው፥ እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደሆነ፥ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም።” / 2ጢሞ. 3፥1.7/ በማለት በመጨረሻው ዘመን የሚነሡ ሰዎችን ፀባይን ይነግረናል፡፡ ይህንን ትምህርተ ጥቅስ ለማገናዘብ  እግዚአብሔርን የማያምነውን ህዝብ ትተን፣ አሁን በዓለም ሁሉ ካለው የቤተ ክርስቲያንዋ አማኞች ብቻ አንጻር በመጠኑ እንይ ደግሞ፤

ሀ. መንፈሳዊ ባህል ማፍረስን ስንመለከት፣ የሁሉንም ባይሆን፣ የአንዳንዶቹ አማኞች ሰዎች ጸባይ ቅ. ጳውሎስ ”ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል” የሚያሰኝ ሕይወት የያዙ እንደሆነ ያስረግጥልናል፡፡ እንደ አማኝ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ፣ ነገር ግን መንፈሳዊ አምልኮ የማይፈጽሙና የራሳቸውን አሳብ ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊጭኑ የሚፈልጉትን ነው ’የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል’ ያላቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቤት መታዘዝ፣ መከባበርና ሰላም የነገሠበት መሆን ነው ያለበት፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ቦታ እንደሚስተዋለው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙዎቹ በመንፈሳዊው ባህል የጠነከሩ እንዳሉ ሁሉ አንዳንዶቹ ሥራ ፈቶች ሆነው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ፖለቲካ፣ዘረኝነት፣አሉባልታ፣ ወዘተ በማምጣት ቤተ ክርስቲያንን ሲያውኩአት ይታያል፡፡ ቅ. ሉቃስ በተመሳሳይ አይሁድ ቀንተው በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረጉትን ”አንዳንዶቹ ተረድተው ከሚያመልኩም ከግሪክ ሰዎች ብዙ ከከበሩትም ሴቶች ጥቂቶች ያይደሉ፥ ከጳውሎስና ከሲላስ ጋር ተባበሩ።  አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ ሕዝብንም ሰብስበው ከተማውን አወኩ፥” /የሐዋ. ሥራ 17፣ 5/ በማለት እንደገለጸው ያሉ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ”ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ፥ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ፥ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና።” ይላቸዋል፡፡

ለ. የክህነት ክብርን ማፍረስ በተመለከተ፣ ቅ. ጳውሎስ ”ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት፥ እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው፥ እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደ ሆነ፥ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም።” እንዳለው ሁሉ ካህናት ነን ከሚሉት ጀምሮ እስከ ምእመናን ድረስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ሰጥቷቸው በአንብሮተ እድ እየተሾሙ ሲወርድ መጥቶ ለኛ የደረሰውን ታላቁን የድኅነት መፈጸሚያ ክህነት እንደ ኢያኔስና ኢያንበሬስ ዛሬ በብዙዎች ተንቆና ተዋርዶ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ ከሚፈጸሙ ስህተቶች ጥቂቶቹን ቀጥለን እንመለከት፣

  • ቅዱስ ማቴዎስ ”በዚያን ዘመን ብዙዎች ይሰናከላሉ፣ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፣ እርስ በርሳቸው ይጣላሉ” /ማቴ. 24፣10/ እንዳለው ሁሉ፤ለዘመናት በአንድነት የኖረችውን ቤተክርስቲያን ”ከዓመጻም ብዛት የተነሣ የብዙዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች” እንዲል፣ በዚህ ዘመን በድፍረት አስተዳደሩዋን በመከፋፈል ”ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት” እንዲሁ አሳድጋ፣ አስተምራ፣ ክህነት የሰጠቻቸውን እናታቸውን ቤተ ክርስቲያን እስከ ማውገዝ የድፍረት ኀጢአት የተደረሰበት ዘመን ነው፡፡በመወጋገዙ ሂደት ያለው ጉዳትን ማን አስተዋለው? እግዚአብሔር ይማረን እንጂ እንደ ሰውኛው ከሆነ፣ በጭካኔ፣ ውስጥ ያለው ውጪውን፣ ውጭ ያለው ደጋግሞ ውስጥ ያለውን አውግዞትአንዲት ነፍስ ወደ እግዚአብሔር እንዳትደርስ ተቆላልፎ ቁጭ ብሏል፡፡ ነገር ግን ኢያኔስና ኢያንበሬስ ሙሴን ቢቃወሙትም ሙሴ ክህነቱ ከእግዚአብሔር በመሆኑ የእግዚአብሔር ክብር በርሱ ላይ ተገልጦ እግዚአብሔርን የተቃወሙት በደላቸው እንደ ተገለጠ ሁሉ፣ ዘለዓለማዊዋ ቤተ ክርስቲያን ክህነታዊ ክብርዋ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ነው፡፡  ”ሁሉ ለንጹሖች ንጹሕ ነው፤ ለርኵሳንና ለማያምኑ ግን ንጹሕ የሆነ ምንም የለም፥ ነገር ግን አእምሮአቸውም ሕሊናቸውም ረክሶአል።  እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፥ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ፥ በሥራቸው ይክዱታል።” / ቲቶ. 1፥15/ እንዳለ፡፡
  • ” ሰለስቱ ምእት በኒቂያ ጉባኤ ’ያለ ኢጲስ ቆጶስ ፈቃድ ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተ ከክህነቱ ይሻር’ብለው ደንግገዋል፡፡ ነገር ግን በተለይ በውጭ አገር እየተለመደ የመጣው ጉዳይ የትኛውንም ኤጲስቆጶስ ሳያስፈቅድ አንድ ካህን፣ ከዚያም አልፎ በሚገርም ሁኔታ ዲያቆን ወይም ምእመን ከፈለገ ቦርድ አቋቋምኩ እያለ ቤተ ክርስቲያን አስተምራ አጥምቃ ያሳደገችውን ምእመን ከሥርዓተ ቤተክርስቲያን በማውጣት እንደ ማንኛውም ድርጅት ቤተ ክርስቲያን ከፈትኩ የሚባልበት የድፍረት ኀጢአት በጠራራ ፀሐይ ከሚፈጸምበት ዘመን ደርሰናል፡፡ በተጨማሪም በዚህ ዓይነት ለተቋቋሙ ሁሉ የሚገለገሉበት ታቦት ከየት መጣ? ሜሮን ከየት ተገኘ? የሚሉ ጥያቄዎች ምላሽ የላቸውም፡፡ ”ብዙዎች ይስታሉ” እንደተባለ በድፈረትና በስሕተት መሠረት ላይ የስሕተትና የድፍረትን ግድግዳ ማቆም፣ የስሕተትና የድፍረት ጣሪያንም ማዋቀር እንደ ሕጋዊ ሥራ ከተቆጠረ ሰነባበተ፡፡
  • የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰው ስፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል” /ማቴ 24፣15/ በየአጥቢያው የሚሰማውን ክፉ ወሬ ስናስተውል የዚህ ትንቢት ተፈጻሚነት እንዳገኘ ያረጋግጥልናል፡፡ የተሐድሶ ሴራ፣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚፈጠሩት ጭቅጭቆች፣ በመነኮሳትና በካህናት የሚነሱ ሐሜቶች፣ ሙሰኝነት፣ዘረኝነት ምን ይነግሩናል?በውጭ አገር በየቦታው አቋቋምን የሚሉት ሰበካ ጉባኤ ሳይሆን ራስ ገዝ የቦርዶቹ አስተዳደር ግፍ ደግሞ በሚገርም ሁኔታ የሚያገለግለው ካህንን የሚያዩት እንደ እግዚአብሔር ካህን ሳይሆን ከአንድ ቅጥር ሠራተኛቸው በታች ነው፡፡ ስለ አስተዳደሩ እንዲያውቅ አይፈልጉም፣ እነሱ ያዘዙትን ብቻ ይሰብካል/ ይናገራል፣ ካህኑም ሲፈልጉ የሚያኖሩት ሲፈልጉ የሚያባርሩት ሆኗል፡፡ ይህን አሠራር ለዘመናት ቤተ ክርስቲያን ከኖረችበት አንጻር ስናየው እጅግ የራቀና አስጸያፊ የሚባል ነው፡፡ ጌታችን ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተው በሥልጣነ ክህነት እንድትተዳደር ሲሆን ይህኛው በተቃራኒ የቆመ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ምእመኑን አስተምራ አጥምቃ አሳድጋ እንደገና በተንኮለኞች ሤራ ልጆቹዋን ቀስጠው በስዋ ላይ እንዲያምጹ ማድረግ የጥፋት ርኩሰት መሆኑን ስንቱ ተረድቶት ይሆን?፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ”ማንም ልዩ ትምህርት የሚያስተምር ከጌታችንም ከኢየሱስ ክርስቶስ በሆነው ጤናማ ቃልና እግዚአብሔርን ለመምሰል በሚስማማ ትምህርት የማይጠጋ ቢሆን፥ በትዕቢት ተነፍቶአል አንዳችም አያውቅም፥ ነገር ግን ምርመራን በቃልም መዋጋትን እንደ በሽተኛ ይናፍቃል፤ ከእነዚህም ቅንዓትና ክርክር ስድብም ክፉ አሳብም እርስ በርስ መናደድም ይወጣሉ፥ አእምሮአቸውም በጠፋባቸው እውነትንም በተቀሙ፥ እግዚአብሔርን መምሰል ማትረፊያ የሚሆን በመሰላቸው ሰዎች ይገኛሉ። እንደነዚህ ካሉት ራቅ።” /1 ጢሞ.6፥3-5/ እንዳለ፡፡

ሐ. ሰብአዊ ክብርና የዕድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና  ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ ለሚለው ሌላ ብዙ ከማለት ይልቅ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ”ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥  ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ” በማለት የዘረዘረው ለርእሰ ጉዳዩ ተስማሚና በቂ ነው፡፡/1ጢሞ.3፥1-3/

ባጠቃላይም የምጽአት ምልክቶች የሚያሳዩት ሁኔታዎች ከመንፈሳዊው እስከ ዓለማዊው፣ ከተማረው እስከ መሀይሙ፣ ከትልቅ እስከ ትንሽ፣ ያላገባው፣ ያገባው፣ መነኩሴው ሳይቀር ሁሉም ሁሉም ባንድ ላይ ከቅድስና ርቀት፣ ከጥፋት ርኩሰት፣ ከመከራ ሕይወት፣ ተቋደሽ መሆናቸውን ነው የሚያሳየው፡፡ ነገር ግን ቅዱሳት መጻሕፍት ተባብረው እንደመሰከሩልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድንገት ይመጣል አይዘገይም፡፡ ቅዱስ ዳዊት ”ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል።  አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይቃጠላል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ።” /መዝ.49፥2-3/ ብሎ እንደተናገረው፡፡ ከላይ እንደተዘረዘረው የሰው ልጆች ሁለ ጊዜ ከመንፈሳውያን እስከ ዓለማውያን ድረስ በተጠመዱበት የዓለማዊ ሥራ እንደ ተወጠሩ ነው ያሉት፡፡ ከዚህም በኋላ የበለጠ በሥጋ ሥራ እየተወጠሩ ይሄዳሉ እንጂ መንፈሳዊ ወደ ሆነው የተጋድሎ ሕይወት የሚያዘነብል ይኖራል ለማለት ያስቸግራል፡፡ እንዲያውም በዐመጽ እየበረታ እስከ መቅደስ ድፍረቱን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይገልጸዋል፤”ማንም በማናቸውም መንገድ አያስታችሁ፤ ክህደቱ አስቀድሞ ሳይመጣና የዓመፅ ሰው እርሱም የጥፋት ልጅ ሳይገለጥ፥ አይደርስምና። እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ አዋጅ እየነገረ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እስኪቀመጥ ድረስ፥ አምላክ ከተባለው ሁሉ፥ ሰዎችም ከሚያመልኩት ሁሉ በላይ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገው ተቃዋሚ እርሱ ነው።” /2ተሰ.2፥3-4/ ይለናል፡፡ ነገር ግን ክርስቲያኖች ነን የምንል ሁሉ የጥፋት ትንቢቱ እኛ ላይ እንዳይፈጸም አሁኑኑ ሳናመነታ ንስሐ መግባትና በትንቢት ከተገለጡት ርኩሰቶች ጨክነን መራቅ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡
 ምንጭ :ማሕበረ ቅዱሳን ድኅረ ገጽ